"In Claris non fit interpretation." (When the text is clear, no interpretation is needed.")
መግቢያ
በዚህ አጭር መነሻ የሆነ የሕግ ማስታወሻ ላይ በተሻሻለው የጸረ ሙስና ልዩ የሥነ ሥርዓትና የማስረጃ ሕግ አዋጅን ለማሻሻል የወጣው አዋጅ ቁጥር 882/2007 አንቀጽ 3(1) ድንጋጌ ዙርያ የቀረበ ሲሆን፤ በተለይም በዚህ ድንጋጌ ስር ስለተመለከተው የዋስትና መብት እና የዋስትና ክልከላ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ያልተያዙ ሰዎችና የተያዙ ሰዎች ላይ የሚተገበርበትን ሁኔታ የመጀመሪያ ምልከታ ለማድረግ ተሞክሯል። ይህንን የሕግ ማስታወሻ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ዋና ጉዳይ አንድ ደንበኛዬ የሆነ ሰው በሙስና ወንጀል ክስ የቀረበበት መሆኑን ከሌላ ሰው ከሰማ በኋላ ጉዳዩን አጣርቶ የሙስና ወንጀል ክሱ የቀረበበት የሙስና ወንጀል ችሎት ዘንድ ባልተያዘበት ሁኔታ በገዛ ፍቃዱ በቀረበ ጊዜ ችሎቱ የአዋጅ ቁጥር 882/2007 አንቀጽ 3(1) ድንጋጌን መሠረት በማድረግ በቂሊንጦ ማረፍያ ቤት ሆኖ ጉዳዩን እንዲከታተል ሲል በቅርቡ የሰጠው ትእዛዝ ነው።