ከሰሞኑ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፍቺን በተመለከተ ለየት ያለ ውሳኔ ተሰጥቷል፡: ይህን ውሳኔ ለሕዝብ ይፋ ቢደረግ ጠቃሚ ሃሳብ እንዲሸራሸር ሊረዳ የሚችል ከመሆኑም በላይ ሕጉንም ለመፈተሸ ይረዳል በሚል አስተያየት ለአንባብያን ለማድረስ እሞክራለሁ፡፡ ጉዳዩ ይፋ ቢሆንም ይግባኝ ሊቀርብበት የሚችል በመሆኑ ለጊዜው የግለሰቦችን ስም ተቀይሯል፡፡ የጉዳዩ ዝርዝር ሁኔታውም ከዚህ በታች ባለው መልኩ ተቀምጧል፡፡
አቶ ሀ እና ወ/ሮ ለ 42 ዓመታት በትዳር ቆይተዋል፡፡ ትዳራቸውም የተደላደለ ነበር፡፡ በዚህ ትዳራቸው ጊዜ ውስጥ ልጅ ያልወለዱ ሲሆን አቶ ሀ ግን ከሌላ የወለዱት አንድ ወንድ ልጅ አላቸው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አቶ ሀ በእድሜ መግፋት (እድሜያቸው 90 ይሆናል) ምክንያት አእምሮአቸው ላይ ከፍተኛ ችግር የተከሰተ በመሆኑ የሚሰሩትን አያውቁም፡፡ የአእምሮ ችግሩን መሰረት በማድረግም የአቶ ሀ ልጅ ወላጅ አባቴ በአእምሮ ችግር የተነሳ የሚሰሩትን አያውቁም በማለት በፍርድ ይከልከሉ፤ የሞግዚትነት ስልጣንም ይሰጠኝ ሲል ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አመለከቱ፡፡ ፍርድ ቤቱም የግለሰቡን የጤና ሁኔታ የሚያሳይ የሕክምና ማስረጃ እንዲቀርብ እና ግለሰቡም በችሎት ቀርበው ሁኔታቸው እንዲታይ በማድረግ ፍርድ ቤቱ ግለሰቡ በራሳቸው ራሳቸውንና ንብረታቸውን ለመቆጣጠር የማይችሉ መሆኑን ተገንዝቧል፡፡ ይህን ተከትሎም ፍርድ ቤቱ አቶ ሀ ላይ የክልከላ (Judicial Interdiction) ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በመቀጠልም የአቶ ሀ ልጅ አሳዳሪና ሞግዚት አድርጎ ሾሟቸዋል፡፡
የአቶ ሀ ልጅም ሞግዚትና አሳዳሪ የሚለውን ሹመት ካገኘ በኋላም ይህንን ሥልጣን መሰረት በማድረግ፣ ሞግዚት አድራጊዬ በእድሜ መግፋት ምክንያት በአእምሮአቸው ላይ የጤና መታወክ የተከሰተ ቢሆንም ተጠሪ ሊንከባከቧቸው አልቻሉም፤ ተለያይተው መኖር ከጀመሩም ረጅም ጊዜ ተቆጥሯል፡፡ ስለዚህ የሞግዚት አድራጊዬና የተጠሪ ጋብቻ እንዲፈርስ ይወሰንልኝ በማለት ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አመልክተዋል፡፡ ወ/ሮ ለ ሞግዚቱ የፍቺ ጥያቄ ይወሰንልኝ ጥያቄ ለማቅረብም ሆነ ፍርድ ቤት ቀርቦ ለመከራከር አይችሉም፣ ለፍቺ የሚያበቃም ምክንያት የለም ሲሉ መቃወሚያና መልስ ሰጥተዋል፡፡
የፌዴራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤትም፣ ሞግዚቱ ጋብቻ እንዲፈርስ ለመጠየቅ ስልጣን አላቸው ወይስ የላቸውም? የግራ ቀኙ ጋብቻ ሊፈርስ ይገባል ወይስ አይገባም? የሚል ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምሮታል፡፡ አንደኛውን ጭብጥ በተመለከተ ፍርድ ቤቱ ሲተነትን
“… በፍ/ብ/ሕ/ቁ. 370(1) መሰረት ሞግዚት አድራጊ ጋብቻ እንዲፈርስ ለመጠየቅ የሚችል መሆኑ ተመልክቷል፡፡ ስለዚህ የአቶ ሀ ሞግዚት የሆኑት ልጃቸው ጋብቻው እንዲፈርስ ለመጠየቅ በሕግ ሥልጣን አላቻው ማለት ነው፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ በወ/ሮ ለ የቀረበውን ሞግዚት አድራጊው ጋብቻ እንዲፈርስ ለመጠየቅ አይችሉም የሚል ክርክርን አልተቀበለውም፡፡”