የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት አዋጅ ከበጎ አድራጎት ኮሚቴ በቀር ለሁሉም የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ሦስት የህልውና ደረጃዎችን ያስቀምጣል፡፡ እነዚህም ምስረታ፣ ምዝገባ እና ፈቃድ ናቸው፡፡ ምስረታ የምንለው የበጎ አድራጎት ድርጅቱን ወይም ማህበሩን ለመፍጠር አስፈላጊ የሚሆኑበት የመጀመሪያ ደረጃ ነው፡፡ የዚህ ደረጃ ዋነኛ መለያው ሶስት ወር ገደማ በሚሆነው በዚህ ጊዜ ውስጥ ድርጅቱ ወይም ማህበሩ ሕጋዊ ሰውነት የሌለውና በሕግ ፊት ውጤት ያላቸውን ተግባራት ለማከናወን ያለው ብቃትም ውሱን መሆኑ ነው፡፡ በተለይም በድርጅቱ ወይም በማህበሩ ስም ገንዘብ የማሰባሰብ ብቃቱ ውሱን ወይም በሕግ የተገደበ ይሆናል፡፡ ይህ የመጀመሪያ ደረጃ ድርጅቱ ወይም ማህበሩ ሲመዘገብ ወይም ባለመመዝገቡ ምክንያት ህልውናውን ሲያጣ የሚጠናቀቅ ይሆናል፡፡
የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ህልውና ቀጣዩ ደረጃ ምዝገባ ሲሆን ድርጅቱ ወይም ማህበሩ በህግ ፊት እውቅና የሚያገኝበት በመሆኑ ከሶስቱ ደረጃዎች ውስጥ ወሳኝ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አንድ ድርጅት ወይም ማህበር በተመዘገበ ጊዜ ሕጋዊ ሰውነት አግኝቶ በሕግ ፊት ውጤት ያላቸውን ተግባራት ለማከናወን ብቁ ይሆናል፡፡ በሌላ አባባል አንድ በመመስረት ላይ የነበረ ድርጅት ወይም ማህበር ሲመዘገብ ውል መዋዋልን የመሰሉ የሕግ ትርጉም ያላቸውን ተግባራት ማከናወን ይችላል፡፡ ለአንድ የበጎ አድራጎት ድርጅት ወይም ማህበር ይህ ማለት ሰራተኞችን በመቅጠር እና ክንውኖችን በመተግበር የተቋቋመበትን ዓላማ ለማስፈፀም የሚያስችል ብቃት በሕግ ፊት ያስገኝለታል ማለት ነው፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቱ ወይም ማህበሩ በሕግ በተቀመጡ ምክንያቶች ካልፈረሰ በቀር ሕጋዊ ሰውነቱን ይዞ ላልተወሰነ ጊዜ ይቆያል፡፡
ይሁን እንጂ ምዝገባ እና ተያይዞ የሚመጣው ሕጋዊ ሰውነት ማግኘት የበጎ አድራጎት ደርጅቱ በሕግ ፊት ውጤት ያላቸውን ተግባራት ለማከናወን ያገኘውን ብቃት እውን ለማድረግ አያበቁትም፡፡ ለዚህ የግድ ፈቃድ ማግኘት አለበት፡፡ ፈቃድ መስጠት ማለት አንድ ደርጅት ወይም ማህበር ባስቀመጠው አካባቢ የተቋቋመበትን ዓላማ ለማስፈጸም ክነውኖችን ወይም ፕሮጀክቶቸን ለመተግበር የሚፈቅድለት ሰርትፍኬት የሚያገኝበት ሂደት ነው፡፡ አንድ ደርጅት ወይም ማህበር በሕግ የተቀመጡ መስፈርቶችን አሟልቶ በተቋቋመ ጊዜ ወዲያውኑ ፈቃድ የሚያገኝ ሲሆን ፈቃዱ በየጊዜው (በየሦስት ዓመት) መታደስ አለበት፡፡
ይህ አጭር ፅሁፍ በሁለት ተዛማጅ ጉዳዮች ላይ ያተኩራል፤ እነዚህም የበጎ አድራጎት ደርጅቶችና ማህበራት ፈቃድ ለማሳደስ ሊሟሉ የሚገባቸው ቅድመ-ሁኔታዎች እና እነዚህ ቅድመ-ሁኔታዎች በዘርፍ አስተዳዳሪዎች የፕሮጀክት ስምምነት ለመፈፀም ከሚጠየቁት መመዘኛዎችና ለጋሾች የገንዘብ ድጋፍ ለመስጠት ከሚያስቀምጧቸው ቅድመ-ሁኔታዎች ጋር ያላቸው ትስስር ናቸው፡፡
ፈቃድ ለማሳደስ ሊሟሉ የሚገባቸው ቅድመ-ሁኔታዎች