በተመሳሳይ ሁኔታ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 259 (2) እና (3) ላይም በፍትሐብሔር ጉዳዮች ላይ ተከራካሪዎች ማስረጃዎቻቸውን አቅርበው ካስረዱ በኋላ ስለክርከሩ ያላቸውን ጠቅላላ ሀሳብ ማቅረብ እንዳለባቸው ተመልክቷል፡፡ ሆኖም አብዛኞቹ የፍትሐብሔር ችሎቶች ተከራካሪዎች ማስረጃዎቻቸውን አቅርበው ከጨረሱ በኋላ ስለክርከሩ ያላቸውን ጠቅላላ ሀሳብ እንዲያቀርቡ አያደርጉም፡፡ እንደውም አንዳንድ የፍትሐብሔር ችሎቶች ላይ ማስረጃዎች ተሰምተው ከተጠናቀቀ በኋላ በተከራካሪ ወገኖች በኩል ስለክርክሩ ያለንን ጠቅላላ ሀሳብ እንድናቀርብ ይፈቀድልን ብለን ስንጠይቅ በመከልከል ፍርድ ተሰጥቷል፡፡ ሆኖም በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕጉ ቁጥር 273 ላይ የፍትሐብሔር ችሎቶች ፍርድ የተከራካሪዎች ማስረጃዎች ተሰምተው ከተጠናቀቁ በኋላ እና ፍርድ ከመስጠታቸው በፊት በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 259 መሠረት የተከራካሪዎችን የማጠቃለያ ሀሳብ ሊቀበሉ እንደሚገባ ያመለክታል፡፡ ሆኖም አብዛኛዎቹ ችሎቶች (በእኔ እይታ እስካሁን ያየኋቸው የፍትሐብሔር ችሎቶች በሙሉ) የፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕጉን ቁጥር 259 (2) እና (3) እንዲሁም 273 ን ተግባራዊ ሲያደርጉ አይታዩም፡፡