ሕግ መንግሥቱን በፖለሲ ማዕቀፍ ሥር?

ሰሞኑን በአንድ ካፌ ገብቼ የተደረደሩ ቀን ያለፈባቸው ጋዜጦች ስመለከት የሪፖርተር ጋዜጣ በሚያዚያ 1/2009 የእለተ-እሁድ እትሙ ላይ “ሰበር ሰሚ ችሎት  በክራውን ሆቴል የንግድ ምልክት ላይ የሰጠው የመጨረሻ ውሳኔ ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም ያስፈልገዋል ተባለ” በሚል ርእስ ባወጣው ዘገባ ላይ ዐይኔ አረፈ። ከዚህ በፊት በርካታ ጉዳዮች ወደ ሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባኤ ስለመቅረባቸው አውቃለሁ። በሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ ላይ የሕገ መንግሥት ጉዳይ ክርክር ተነስቶበት ወደ ጉባኤው ስለመቅረቡ ሳነብ ግን የመጀመሪያዬ ነው።  ምናልባት እኔ ያላወቅኳዋቸው ተመሳሳይ ጉዳዮች ከዚህ በፊት ቀርበው ይሆናል። ያም ሆነ ይህ ርእሰ ጉዳዩ ቀልቤን ስለሳበው ባለጉዳዮቹ  ስለተከራከሩበት ጉዳይና የችሎቱ ውሰኔ  ለማወቅ ጉጉት አደረብኝ። እናም  ወደ ሕገ መንግሥት አጣሪ ጉባኤ ስለተወሰደው የሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔና ስለክርክሩ ከሥሩ ለማየት ወሰንኩ። ስለሆነም የሰበር ሰሚ ችሎት ውሳኔ ቅጂ ፈልጌ በመመልከት የሚከተለውን  የግል እስተያየቴን ለመጻፍ ውደድኩኝ።

ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም ያስፈልገዋል የተባለው ውሳኔ ምንነት

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ውሰኔ የሰጠበት ጉዳይ በክራውን ሆቴል  ባለቤት (አመልካች) እና ሲክስ ኮንትኔታል ሆቴልስ (ተጠሪ) ከ2006 ዓ.ም ጀመሮ ከአእምሮ ንብረት ጽሕፈት እሰከ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ብሎም ወደ ሰበር ሰሚ ችሎት የቀረበ  ክርክር ነው። ይህ የመዝገብ ቁጥሩ 117013 የሆነውና ሰበር ሰሚ ችሎቱ በሰኔ 22 ቀን 2008 በዋለውና አምስት ዳኞች በተሰየሙበት ችሎት የተወሰነው ውሳኔ ከንግድ ምልክት ጥበቃ ጋር የተያየዘ ክርክር ነው። ወደ ሰበር ሰሚ ችሎት የቀረበው ጉዳይ ከንግድ ምልክት ምዝገባ  ተቃውሞ ጋር በተያየዘ የክራውን ሆቴል ባለቤት በአእምሮ ጽሕፈት ቤት ውሰኔ ቅር ተሰኝተው ለከፈተኛ ፍርድ ቤት ይገባኝ ያሉበት ጉዳይ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የእእምሮ ጽሕፈት ቤት ውሳኔውን ስለኣጸና የፍርድ ቤቱ ውሳኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ ይታረምልኝ በማለት ሲሆን፤ ሰበር ሰሚ ችሎቱም ጉዳዩን ከስር መሰረቱ በመፈተሽ መሠረታዊ የሕግ ስህተት አለበት ብሎ ለአመልካች ወስኗል። 

ጉዳዩ ከመሰረቱ ሲታይ በወርሃ ነሃሴ 2005 “CROWNE PLAZA” በሚል በተጠሪ በኩል  በቀረበው የንግድ ምልክት ምዝገባ ጥያቄ ላይ ተቃውሞ ካለ በቀረበው የጋዜጣ ጥሪ መሠረት አመልካች (CROWN HOTEL) በቃልና በጽሁፍ በተደጋጋሚ ተቃውሞ ያቀርባሉ። ለተቃውሞ ምክንያት የሆነው በሕግ ጠበቃ ያገኘውን የንግድ ምልክት የቀዳሚነት መብቴን ይጥሳል የሚል ነው። ተቃውሞው የተመሠረተው በአዋጅ 501/ 2005 አንቀጽ 6 እና  አንቀጽ 7 መሠረት ሲሆን በተለይም በአንቀጽ 7(1) “ከአንድ ዓይነት ወይም ተመሳሳይ እቃዎች ወይም አግልግሎቶች  ጋር የተያያዘ  የሌላ ሰው ቀዳሚ የንግድ ምልክት ጋር አንድ ዓይነት ወይም መሳከርን ሊያስከትል ተመሳሳይነት ያለው”  ሲሆን ለምዝጋባ በቁ አይደለም ብሎ በሚደነግገው መሠረት እንዲሁም በተጨማሪም በንግድ ምዝጋባ አዋጅ 686/2002 አንቀጽ 24 (3) (ሀ) መሠረት የንግድ መዝጋቢው አካል “ቀደም ሲል ከተመዘገቡት የንግድ ስሞች ጋር አንድ ዓይነት ወይም ተመሳሳይና አሳሳች አለመሆን  24 (3) (በ) መሠረት ደግሞ በንግድ ስም መዝገብ  በተመዘገበ የንግድ ስም ላይ ላይ ከፊቱ ወይም ከኋላው ቃላት በመጨመር ያልቀረበ መሆኑን በማረጋገጥ እንዲመዘገብ በሚደነግገው መሠረት ቀደም ሲል ተመዝግቦ ሥራ ላይ ካለው CROWN HOTEL+ logo ጋር ይመሳሰል። በዚህም በሕግ ጥበቃ ያገኘው መልካም ስሜና ዝናዬ ይነካል የሚል ነበር። እውነት ነው የእእመሮ ንብረት ጽሕፈት ቤት ትኩረት የንግድ ምልክቱ ወይም የፈጠራው ጉዳይ ላይ ሲሆን የንግድ መዝጋቢው አካል ደግሞ በንግድ ስሙ ላይ ያተኩራል። ቀዳሚነት ያለው የንግድ ምልክት “CROWN HOTEL” የሚል ሲሆን፤ አዲሱ የንግድ ምልክት “CROWNE PLAZA” የሚል ነው። የተጨመሩት ነገሮች በ CROWN ላይ” E”  እንዲሁም “PLAZA”  የሚለው ቃል ነው።  ሁሉቱም የሆቴል አግልግሎት ሰጪዎች መሆናቸው ልብ ይሏል። በክርከር ሂደቱ በርካታ ጭብጦት ለክርክር ቀርበው የነበረ ሲሆን የዚህ ጽሑፍ ዓላማ በክርክር ሂደቱ በጭብጥነት ተይዞ እስከ መጨረሻ በዘለቀው  ጭብጥ ላይ ብቻ  የሚያተኵር ይሆናል። 

በፍርድ ሃተታው እንደተመለከተው በአመልካች በኩል ለተቃውሞ መነሻ የሆኑት የሕግ መሰረቶች  የንግድ ምዝገባ አዋጅ እና የንግድ ምልክት ምዝጋባ አዎጅ ሲሆኑ  ጽሕፈት ቤቱ በመጀመሪያ  ተቃውሞውን  ከአዋጅ 501/ 1998 ጋር በማገናዘብ ተቀበሎ የምዝገባ ሂደቱን አቋረጦ የነበረ ቢሆንም ለሁለተኛ ጊዜ ውሳኔውን ሊቀለበሰው ችሏል። ውሳኔው ለአመልካች ከተነገረ በኋላ እንደገና ውሰኔውን በመቀየር የሚከተሉት ምክንያቶችን አቅርቧል። ጽሕፈት ቤቱ የንግድ ምልክቶቹ መመሳሰል ሳይክድ ኢንቨስትመነትን ለማበረታት ይጠቅማል በሚል ሁለቱም የንግድ ምልክቶች እንዲቀጥሉ ወስኗል። አክሎም ጽሕፈት ቤቱ ውሳኔው እንዳይደገም ራሱን አስጠንቅቆ ዘግቶታል። ይህም ውሰኔው ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት ካለው ፍላጎት ውጭ ተገቢ እንዳለሆን ያመነበት ይመስላል። ምክንያቱ ይህንን ውሳኔ ከሰጠ በኋላ ተመሳሰይ ውሳኔ እንዳይደገም በራሱ ላይ እግድ አስቀምጧል። እዚህ ላይ ሊነሳ የሚቸለው ጥያቄ ውሳኔው ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት እስከ ሆነ ድርስ የማይደገመበት ምክንያት ምንድ ነው? ከአዲሱ ድርጅት የተሻለ ኢንቨስትመነት ይዘው በተመሳሳይ  የንግድ ምልክት ለሚቀርቡ ባለሃብቶችስ ምን ዓይነት ምላሽ ሊስጥ ነው? ዜጎችን በእኩልና ፍታሃዊ መንገድ ሊያገልግል የቋቋመ ተቋም ልክ እንዳልሆነ አምኖ እንዳይደገም የሚለውን ውሳኔ እንዴት ሊወስን ይችላል? CRROWN HOTELS and Convention Center የሚል የንግድ ምልክት ይዞ ከቀደሙት ሁለቱ ሆቴሎች ይልቅ የተሻለ አቅም ያለው ባለሀብት ለምዝገባ ቢያመለክትስ? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳት ይቻላል።

Continue reading
  14693 Hits