አንዳንድ ነጥቦች ስለአዲሱ የመንገድ ትራፊክ መቆጣጠሪያ ማሻሻያ ደንብ ቁጥር 395/2009

በየካቲት ወር 2008 ዓ/ም መዲናችን አዲስ አበባ ላይ የመንገድ ትራንስፖርት ትራፊክ መቆጣጠሪያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 208/2003 ዓ/ም የሪከርድ አያያዝ ትግበራ መጀመሩን ተከትሎ የታክሲ የአሽከርካሪዎች ስራ የማቆም አድማ ነበረ፡፡ በዚህም መሰረት ተግባራዊ መደረግ ተጀምሮ የነበረው የሪከርድ አያያዝ ተግባራዊነቱ እንዲቋረጥ ተደርጎ ከአሽከርካሪዎች እና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ከተደረገ በኋላ የደንቡ መሻሻል አስፈላጊነት ታምኖበት ደንቡ እንዲሻሻል ተደርጓል፡፡ በወቅቱ በአሽከርካሪዎች በኩል ሀገሪቱ ባላት የትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ብቃት ደረጃ፣ የመንገድ መሰረተ ልማት ችግሮች፣ ልል የሆነ የትራፊክ ተቆጣጣሪዎች ተጠያቂነት፣ የተቆጣጣሪዎች ስነምግባር ችግር እንዲሁም ከብዙ ተያያዥ ጉዳዮች ጋር በተገናኘ በደንብ ቁጥር 208/2003 ዓ/ም ላይ ሪከርድን የሚመለከተው ክፍል ወደ ተግባር የሚገባ ከሆነ አስቸጋሪ ሁኔታዎች እንደሚፈጠርባቸው ለስራ ማቆም አድማው የተሰጡት ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ደንቡ በ2003 ዓ/ም እንደመውጣቱ እሪከርድን የሚመለከተው ክፍል ተግባራዊ መደረግ የጀመረው በ2008 ዓ/ም መሆኑ በራሱ የህግ አስፈጻሚውን ቸልተኝነት የሚያሳይ ሲሆን ደንቡን በመተግበር ረገድ ቀድመው የጀመሩ እንደ አማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ያሉትን ደግሞ በክልላቸው የሚንቀሳቀሱትን አሽከርካሪዎች በሀገሪቷ ውስጥ ካሉ ሌሎች አሽከርካሪዎች በተለየ ሁኔታ ተጎጂ ሲያደርጋቸው ነበር፡፡ ይህ ጽሁፍ ደንቡ የተሻሻለበትን ምክንያቶች አግባብነት፣ ማሻሻያው ውስጥ የተጨመሩ እና ማስተካከያ የተደረገባቸውን አንቀጾች እንዲሁም የማሻሻያውን አንድምታ በተወሰነ መልኩ ለመዳሰስ ይሞክራል፡፡

  25290 Hits