አላግባብ/በስህተት የተከፈለን የጡረታ አበል ለማስመለስ የሚቀርብ ክስን የሚያስቀረዉ የይርጋ ዘመን ምን ያህል ነዉ?

መግቢያ

የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት በሰበር ችሎት ዉሳኔዎች ቅጽ 14 መግቢያ እንዲህ ሲሉ ተናግረዋል፤ “ለተመሣሣይ ጉዳዮች በጣም የተራራቁ ዉሣኔዎችን በመስጠት ይታይ የነበረዉን ችግር በመቅረፍና የዉሣኔዎችን ተገማችነት በማረጋገጥ ረገድ የሰበር ዉሣኔዎች አስገዳጅ መሆን ከፍተኛ ዉጤት አስገኝቷል ማለት ይቻላል፡፡ አልፎ አልፎ በዉሣኔዎች ጥራትና ስርጭት ሊታዩ የሚችሉ ችግሮች ሥርዓቱ እየተጠናከረ ሲሄድ የሚፈቱ ሲሆን አነዚህን ችግሮች ለማቃለል እኛም ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን፡፡ ጥረታችን ሊሳካ የሚችለዉ በዉሣኔዎቹ ላይ በሕግ ምሁራንና ባለሙያዎች ገንቢ የሆኑ ትችቶችና አስተያየቶች ሲቀርቡ ነዉ”፡፡ እኔም ይህን ግብዣ በመቀበል የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ችሎት ሕዳር 21 ቀን 2005 ዓ.ም. በሰጠዉ ዉሳኔ ላይ ትችቴን ከዚህ በመቀጠል አቀርባለሁ፡፡ ዉሳኔዉ የተሰጠዉ በማኅበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ እና ታዬ አበራ መካከል ባለዉ ክርክር በሰበር መዝገብ ቁጥር 72341 ነዉ፡፡ በዚህ መዝገብ ከተነሱት ዋነኛ ጉዳዮች ዉስጥ፤ አላግባብ የተከፈለ ጡረታን ለማስመለስ የሚቀርብ ክስ በይርጋ ይታገዳል ወይ፤ ከታገደስ የይርጋ ዘመኑ ምን ያህል ነዉ የሚሉት ይገኙበታል፡፡

የጉዳዩ መነሻ

አቶ ታዬ አበራ ከግንቦት 01 ቀን 1984 ዓ.ም. ጀምሮ በየወሩ የጡረታ አበል ይወስዱ ነበር፡፡ ከሰኔ 01 ቀን 1989 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ በመንግስት መስሪያ ቤት ተቀጥረዉ ደመዎዝ ተከፍሏቸዋል፡፡ አቶ ታዬ የጡረታ አበላቸዉን መዉሰዳቸዉንም እንደቀጠሉበት ነዉ፡፡ የመንግስት ሰራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁጥር 209/1955 አንቀጽ 30(2) እና በመንግስት ሰራተኞች ጡረታ አዋጅ ቁጥር 345/1995 አንቀጽ 46(1) መሰረት፡ የአገልግሎት የጡረታ አበል በመቀበል ላይ ያለ ባለመብት እንደገና በመንግስት መሥሪያ ቤት ተቀጥሮ ደመዎዝ ማግኘት ከጀመረ አበሉ ይቋረጣል፡፡ በመሆኑም በማኅበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ የተጠየቀዉ ዳኝነት እነዚህን ያጠቃልላል፡፡ 1) ከሰኔ 01 ቀን 1989 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ነሐሴ 30 ቀን 1995 ዓ.ም. ድረስ በየወሩ ብር 105.00 የወሰዱት ለሰባ አምስት ወራት ያህል ተባዝቶ የሚመጣዉን ዉጤት ብር 7575.00፤ 2) ከሐምሌ 01 ቀን 1996 ዓ.ም. እስከ ሀምሌ 01 ቀን 1998 ድረስ በየወሩ ብር 115.50 የወሰዱት ታስቦ የሚመጣዉን ድምር ብር 4045.50፤ 3) ወጪና ኪሳራ እንዲሁም ከሕጋዊ ወለዱ ጋር እንዲከፍሉ፡፡ የማኅበራዊ ዋስትና ኤጀንሲ ለመጀመሪያ ጊዜ ክስ የተመሰረተዉ በጥቅምት 18 ቀን 2003 ዓ.ም. ነዉ፡፡

የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ዉሳኔ

Continue reading
  9194 Hits