የማስረጃ ሕግ - ሕጉ እና አተገባበሩ

በሰዎች የእለት ከዕለት መስተጋብር ዉስጥ ከሚፈጠሩ ነገሮች መካከል አንዱ ቅራኔ ነዉ። ቅራኔ ሲኖር ደግሞ የመረጃ ወይም ማስረጃ ጉዳይ አብሮ ይነሳል። በተለይ ለዳኝነት አካላት ማለትም ለፍርድ ቤት፤ ለግልግል እና ለመሳሰሉት በሚቀርቡ ክርክሮች ላይ ማስረጃን ወይም መረጃን የሚመለከቱ ጉዳዮች መነሳታቸዉ አይቀሬ ናቸዉ። እዚህ ላይ የመረጃ እና ማስረጃን ልዩነት መረዳት ተገቢ ነዉ። ማስረጃ አንድን አከራካሪ ፍሬ ጉዳይ ለማረጋገጥ ወይም ለማስተባበል የሚቀርብ ተጨባጭ ጉዳይ ሲሆን፤ መረጃ ግን አንድን ነገር ለማረጋገጥ ወይም ለማስተባበል የሚሰጥ መግለጫ (Information) ብቻ ነዉ። ሁሉም ማስረጃ የመረጃነት ባህሪ ያለዉ ሲሆን፤ ሁሉም መረጃ ግን ማስረጃ አይደለም። ማስረጃ ለፍትሕ አካል የሚቀርብ መረጃ ሲሆን፤ ይህ መረጃም ፍሬ ነገርን የሚመለከት ነዉ። ፍሬ ነገር ማለትም በፍርድ ቤት ወይም በሌላ የዳኝነት አካል ፊት አከራካሪ ሆኖ የወጣ እና የተያዘ ጭብጥን የሚመለከት ነዉ። ማስረጃ የሚቀርበዉም ይህንን አከራካሪ ጭብጥ ወይም ፍሬ ነገር ለማረጋገጥ ወይም ለማስተባበል ነዉ። የማስረጃ ሕግ ተፈጻሚነት የሚታየዉም በዚህ ጊዜ ነዉ።

  4242 Hits

ስለማስረጃ ሕግ አደረጃጀት

የማስረጃ ሕግ የማስረጃን አግባብነት፣ የማስረጃን ተቀባይነት እንዲሁም የማስረጃን ክብደትና ብቃት የሚገዙ ደንቦችና መርሆዎች ጥርቅም ነው፡፡ ማስረጃ ተሟጋቾች በአቤቱታቸው አማካኝነት ፍርድ ቤት የያዘውን ጭብጥ የሚያረጋግጡበት ዘዴ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ማስረጃ ማለት ፍርድ ቤት የያዘውን አከራካሪ ጉዳይ ወይም ጭብጥ በሚሰማበት ጊዜ ተሟጋቾች የጥያቄውን አግባብነት፣ እውነትነት፣ በምስክሮች፣ በሠነድ፣ ተጨባጭነት ባላቸው ሌሎች ነገሮች፣ ወዘተ… ማስረጃ ለፍርድ ቤቱ የሚያረጋግጡበት አሊያም ውድቅ የሚያደርጉበት ዘዴ ነው፡፡ ማስረጃ ሲባል የአንድን ፍሬ ነገር ህልው መሆን ወይም አለመሆን ለማረጋገጥ ያገለግል ዘንድ ክስ በሚሰማበት ጊዜ ወይም የክርክር ጭብጥ በሚጣራበት ወቅት በተከራካሪ ወገኖች ወይም ክርክሩን በሚያየው ፍርድ ቤት ትዕዛዝ አማካኝነት የሚቀርብ ማናቸውም ዓይነት የአስረጂነት ባህርይ ያለው ነገር ነው፡፡ ማስረጃ በምስክሮች (Witnesses)፣ በዘገባ (Record)፣ በሠነድ (Document)፣ ተጨባጭነት ባላቸው ሊታዩ ሊዳሰሱ በሚችሉ ነገሮች (Concrete Objects) እና በኤግዚቢት መልክ ሊቀርብ ይቸላል፡፡ አቀራረቡም በሕግ በተደነገገው ሥርዓት መሠረት ነው፡፡ የክርክሩን ጭብጥ ፍሬ ነገር እውነት ወይም ሀሰት መሆኑን የማሳመን ኃይል ያለው እንደመሆኑ እና በዚህም ወደ ውሳኔ የሚያደርሰው ስለሆነ ሊገኝም ሊቀርብም የሚገባው በሕግ አግባብ ነው፡፡ ማስረጃው ተቀባይነት ወይም ውድቅ የሚደረገው እንደዚሁም ሊሰጠው የሚገባው ክብደት የሚመዘነውም በሕግ አግባብ ነው፡፡

  18297 Hits