የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የቀረቡትን የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤትና የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንቶችን ሹመት አፀደቀ።
በዚህ መሠረት አቶ በላቸው አኑቺሳ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት እንዲሁም አቶ መሀመድ አህመድ የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው ተሹመዋል።
አቶ በላቸው ከኮተቤ መምህራን ኮሌጅ ዲፕሎማ፣ ከሲቨል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፀጥታና ደህንነት ሁለተኛ ዲግሪ አላቸው።
በፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ በደቡብ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤትና በደቡብ ክልል ሃድያ ዞን በዳኝነት እንዲሁም በደቡብ ክልል ፍትሕ ቢሮ የሃድያ ዞን ፍትሕ መምሪያ ሃላፊ ሆነው በመስራት አገልግለዋል።
የፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙት አቶ መሀመድ አህመድ ደግሞ የመጀመሪያ ዲግሪ በሕግ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ከሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል።
በፍትሕ ሚኒስቴር በረዳት ዓቃቤ ሕግ ደረጃ የዜጎች ቅሬታ አገልግሎት ማስተናገጃና ሥነ ምግባር ክትትል ኃላፊ፣ የሕግ ጥናት ማርቀቅና ማስረጽ ዳይሬክተር በመሆን እንዲሁም በደቡብ ሱዳን ብሔራዊ ሸንጎ የሕግ አርቃቂ በመሆን ሰርተዋል።
ወይዘሮ ለሊሳ ደሳለኝና አቶ በሪሁን ተወልደብርሃን ደግሞ የከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው ተሹመዋል።
መልካም የሥራ ዘመን ይሁንላቸው ብለናል፡፡