ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም የተጠየቀበት የእነ አቶ መላኩ ፈንታ የክስ ይነሳልን አቤቱታ ከሕገ መንግሥታዊ ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም አያስፈልገውም ተባለ።
ለፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አዲሱን የጉሙሩክ አዋጅ 859/2006 አንቀጽ 182ን በመጥቀስ ክስ ይነሳልን ወይም ይቋረጥልን በማለት አቤቱታ ያቀረቡት አቶ መላኩ ፈንታ እና አቶ ገብረዋህድ ወልደጊዮርጊስን ጨምሮ 8 ግለሰቦችና 5 ኩባንያዎች ናቸው።
ለአቤቱታቸው መነሻ የሆናቸው በዚህ በተሻሻለው የጉሙሩክ አዋጅ ከጉሙሩክ ማጭበርበርና ከቀረጥ ነጻ መብት ያለአግባብ መጠቀም የሚሉ ወንጀሎች በአስተዳደራዊ ውሳኔ እና በገንዘብ መቀጮ ይታለፉ የሚል ነው።
በዚሁ አዋጅ አንቀጽ 182 አዲሱ አዋጅ ከጸናበት ቀን በፊት የተጀመሩ ጉዳዮች በነበረው ሕግ መሠረት ፍጻሜ ያገኛሉ ሲል፣ የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 22 ንዑስ ቁጥር 2 ደግሞ ድርጊቱ ከተፈጸመ በኋላ የወጣ ሕግ ለተከሳሹ ጠቃሚ ሆኖ ከተገኘ ከድርጊቱ በኋላ የወጣው ሕግ ተፈጻሚነት ይኖረዋል ይላል።
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ የወንጀል ችሎትም አዋጁ ከሕገ መንግሥቱ ጋር ተቃርኖ አለው በማለት ነበር ለሕገ መንግሥታዊ ትርጉም ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት የላከው።
በዚህም መሠረት የሕገ መንግሥታዊ አጣሪ ጉዳዮች ጉባኤ ሐምሌ 17 ቀን 2007 ዓ.ም ጉባኤ ተቀምጦ የቀረበውን የፍርድ ቤት ትዕዛዝ መርምሮ፣ አዋጁ በዋነኝነት መተርጎም ያለበት ከአዋጁ አጠቃላይ ዓላማ አንጻር ነው የሚለውን ዋነኛ ማጠንጠኛ አድርጎታል።
ጉባኤው አዋጁ ጠንካራ የሕግ ማስከበሪያ ሥርዓት ዘረጋ እንጅ በቀድሞው ሕግ ለተቀጡ ወይም ለተከሰሱ ሰዎች ይጠቅማል ወይም አይጠቅምም የሚለውን መነሻ አላደረገም የሚለውንም ተመልክቷል።
በአዋጅ ቁጥር 859/2006 የመሸጋገሪያ ድንጋጌ ውስጥ የተቀመጠው ጉዳይ በግልጽ ሕጎችን ተፈጻሚነት በመጠበቅ በአዋጁ መግቢያ ላይ የተቀመጠውን ዓላማ ለማሳካት ሕግ አውጭው ታሳቢ ያደረገውና ቀደም ሲል የተጀመሩ ክሶች ባሉበት እንዲቀጥሉ በግልጽ ለማስቀመጥ ነው ሲል ጉባኤው አትቷል።
ሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 22 ንዑስ ቁጥር 2 ድርጊቱ ከተፈጸመ በኋላ የወጣው ሕግ ለተከሳሽ ወይም ለተቀጣው ግለሰብ ጠቃሚ ሆኖ ከተገኘ ከድርጊቱ በኋላ የወጣው ሕግ ተፈጻሚነት ይኖረዋል በማለት ነው የደነገገው።
አዲሱ አዋጅ ተከሳሾች እንዳይጠቀሙ ያላደረገ በመሆኑ አዋጁ ከሕገ መንግሥቱ ጋር አይቃረንም ሲልም ነው ጉባኤው ያመለከተው።
የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ሕገ መንግሥታዊ ትርጉም ያስፈልገዋል በማለት የላከውን ብይን፤ ጉባኤው በአብላጫ ድምጽ የሕጉ አጠቃላይ ትርጉም መነሻ የሚያደርገው የአዋጁን አጠቃላይ ዓላማ በመሆኑ ጉዳዩ የሕገ መንግሥት ትርጉም አያስፈልገውም ብሏል።
ችሎቱ ዛሬ ከጉባኤው የተላከውን ውሳኔ በንባብ ካሰማ በኋላ ብይን ለመስጠት ለነሐሴ 13 ቀን 2007 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።
ከዚህም ሌላ በመዝገቡ የተካተቱት ዶክተር ፍቅሩ ማህሩ ጉዳዩ ተነጥሎ ይታይልኝ በማለት ያቀረቡት አቤቱታ እልባት በማጣቱ ቅሬታቸውን አቅርበዋል።
በተመሳሳይም ኬኬ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር በጠበቃው አማካኝነት ቅሬታ አቅርቧል፤ ፍርድ ቤቱም በዳኛ መጓደል ምክንያት አቤቱታ አቅራቢዎቹ ምላሽ ማጣታቸውን ጠቅሶ በቅርቡ ዳኛ ሲሟላ አቤቱታቸው ምላሽ ያገኛል በማለት መልስ ሰጥቷል።
አቢሲኒያ ሎው ይህንን በሚመለከት ቀጣይ የሕግ ትንታኔ ይዞ የሚቀርብ ሲሆን በዚህ ጉዳይ አስተያየት ወይም ጽሑፍ አለኝ የምትሉ በThis email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ብትልኩልን ደስተኞች ነን፡፡