- Details
- Category: Property Law
- Hits: 9203
የዚህ ቃል (Usucaption) ትርጉም አንድ ነገር በመጠቀም ባለቤት መሆን ማለት ነው (acquired by usage) ። ይህ የሃብት ማግኛ መንገድ ተፈፃሚ የሚሆነው በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ ብቻ ሆኖ በተከታታይ ረዘም ላለ ጊዜ የተጠቀመበት እንደሆነ የሚገኝ የባለሃብትነት መብት ነው።
አንድ ነገር በመጠቀም ባለሃብት መሆን ክስ ከሚቀርብበት የይርጋ ጊዜ የተለየ ፅንስ ሓሳብ ነው።
ሀ/ የይርጋ ጊዜ (period of limitation) ማለት አንድ በንብረት ላይ መብት ያለው ሰው መብቱን ሲነካበት መብቱን በነካ ሰው ላይ ክስ የሚያቀርብበት የጊዜ ገደብ ሆኖ፤ ይህ የጊዜ ገደብ ካለፈ በኃላ ክስ ያቀረበ እንደሆነ ግን ከተከሳሽ ወገን ተቃውሞ ሊገጥመው እንደሚችል ነው።
ለ/ ባለሃብትነት የሚያቋርጥና የሚያሰገኝ የይርጋ ጊዜ (Acquisitive prescription and extinctive prescription)
- 1.የባለሃብትነት መብት እንዲቋርጥ የሚያደርግ የይርጋ ጊዜ ፤ ይህ የይርጋ ጊዜ አንድ ሰው በአንድ ንብረት ላይ የነበረው የባለሃብትነት መብት የሚቋረጥበት ሁኔታ የሚያመለክት ሆኖ ባለሃብትነቱ ሲቋርጥ ጊዜም ሌላ መተኪያ መብት የማይገኝበት ነው ለምሳሌ፦ ፍ/ሕግ ቁ.1192፣
- 2.የባለሃበትነት መብት ማግኛ የይርጋ ጊዜ (usucaption) ፤ ይህ የይርጋ ጊዜ ደግሞ ለሌላ አዲስ ሰው የባለሃብትነት መብት የሚያስጨብጥ ነው። የይርጋ ጊዜ ርዝመቱ ከአገር አገር ሊለያይ የሚችል ነው። ለምሳሌ የፈረንሳይና ጀርመን የ30 ዓመት የይርጋ ጊዜ አላቸው። ይህ ብቻ ሳይሆን ንብረቱ በቅን ልቦና የያዘው መሆን እንዳለበትም እንደ ተጨማሪ መለኪያ ይጠቀማሉ።
በኢትዮጵያ ፍ/ሕግ በቁጥር 1168 ላይ ከላይ የተመለከትነው የይርጋ ጊዜ (usucaption) ተደንግጎ ይገኛል። ይኸውም የአንድ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለይዞታ በመሆን ለተከታታይና ለ15 ዓመታት ያህል ያለማቋረጥ በሰሙ ግብር እየከፈለበት የቆየ ሰው የዚህ ንብረት ባለሃብት እንደሚሆን ነው። የፍ/ሕጉ በወጣበት ወቅት ይህ ድንጋጌ በመሬትና በህንፃዎች ላይ ተፈፃሚ እንዲሆን ታስቦ የተደነገገና የፊዩዳሉ ስርዓት እስከተገረሰሰበት ጊዜ ድረስ ተግባራዊ ሲደረግ የነበረ ነው። መሬት የመንግስት ንብረት እንዲሆን ከታወጀበት ጊዜ ጀምሮ ግን ድንጋጌው በህንፃዎች ላይ ብቻ ካልሆነ በስተቀር በመሬት ላይ ተፈፃሚ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ እንደሌለ ነው። እንዲሁም ድንጋጌው ለህዝብ ጥቅም ተብለው በተመደቡ ንብረቶች እና በአለባ ምክንያት በተያዙ የማይንቀሳቀሱ ንብረቶች ላይ ተፈፃሚነት የለውም (ፍ/ሕግ ቁ.1455 ፣ 1314 ይመለከተዋል)።
እዚህ ላይ ሊነሳ የሚችለው ጥያቄ አንድ ሰው የራሱ ያልሆነ የማይንቀሳቀስ ንብረት እንዴት አድርጎ ግብር ሊከፍልበት ይችላል የሚል ነው። ይህ ሁኔታ በተለያየ ምክንያት ሊከሰት ይችላል። ለምሳሌ ፦ በማታለል ወይም ባገኘው የውከልና ስልጣን ተጠቅሞ ወይም የጋራ ሃብት የሆነውን ንብረት በመያዙ ምክንያት በስሙ ግብር እየከፈለበት ለተከታታይ 15ዓመት የቆየ እንደሆነ ወዘተ መጥቀስ ይቻላል።
ቁጥር 1168 ስር የተቀመጠው የ15 ዓመት የይርጋ ጊዘ (ሃብት የሚገኝበት ይርጋ) ሊቋረጥ የሚችለው በፍ/ሕግ ቁጥር 1851-1852 መሰረት መሆኑን ግንዛቤ ሊወስድበት ይገባል።
የዋና ተጨማሪ ነገር (Accession)
የዋና ተጨማሪ ነገር አራተኛው የሃብት ማግኛ መንገድ ነው። የፍ/ሄር ሕጋችን የዚህ ትርጉም ባያስቀምጥም ከአጠቃላይ ይዘቱ ተነስተን ሰናየው ግን አንድ ባለሃብት በነበረው ንብረት ወይም ሃብት ላይ ሌላ ሃብት ሲጨመርለት የሚያመለክት ነው። ይህ የተጨመረ ነገር በተፈጥሮ ሓይል ወይም በሰው ጉልበት አማካኝነት የመጣ ሊሆን ይችላል። የእነዚህ ተጨማሪ ነገሮች ባለሃብት ደግሞ የዋናው ነገር ባለሃብት የሆነው ሰው ነው። ይህ ተጨማሪ ነገር በሚንቀሳቀስ ወይም በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ ሊከሰት ይችላል።
ሀ/ የማይንቀሳቀስ ንብረት በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ ሲጨመር፤ ይኸውም በሁለት መንገድ ሊፈፀም ይችላል።
- 1.ጐርፍ ጠርጎ ያመጣውን አፈር በሌላ ሰው መሬት ላይ ሲያርፍ የዚሁ መሬት ባለቤት ሃብት ይሆናል። (Alluvium ይሉታል) ።
- 2.ጐርፍ አቅጣጫው ቀይሮ ሲሄድ ከአሁን በፊት የጐርፍ መሄጃ የነበረ ቦታ ሊታረስ ወይም ለሌላ ጥቅም ሊውል የሚችል ቦታ ስለሚሆን በአቅራቢያው ያለ ባለ መሬት የዚያ ቦታም ባለሃብት ይሆናል። (Accretion ይሉታል) ።
እዚህ ላይ መስተዋል ያለበት ግን በአገራችን የመሬት ባለቤት መንግስትና ህዝብ በመሆናቸው የመሬት ባለቤት ከማለት የልቅ ባለይዞታ ቢባል የተሻለ ይሆናል።
ለ/ ተንቀሳቃሽ ንብረት በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ ሲጨመር
የዚህ ዓይነት ሁኔታ ሊከሰት የሚችለው አንድ ተንቀሳቃሽ ንብረት የአንድ የማይንቀሳቀስ ንብረት ሙሉ ክፍል (intrinsic element) ሲሆን ነው። ይህ በራሱ በሁለት መንገድ ይፈፀማል።
- 1.አንድ የሚንቀሳቀስ ንብረት ባለሃብት የሌላ ሰው ሃብት ከሆነው የማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ በማደባለቅ ሙሉ ክፍል ሲያደርገው ነው። ለምሳሌ፦ አንድ ሰው በሌላ ሰው መሬት ላይ እህል የዘራ ወይም ዛፍ የተከለ እንደሆነ ወይም ህንፃ የገነባ እንደሆነ ጉዳዩ መታየት ያለበት ይህ ስራ ሊያከናውን የቻለው በባለመሬቱ ፈቃድ ነው ወይስ አይደለም? ባለመሬቱ እየተቃወመ ባለበት ሁኔታ ወይስ ሳይቃወመው ነው? የሚሉትን ጥያቄዎች በቅድሚያ በመመርመር ነው።
እዚህ ላይ ትኩረት የሚሻ ነጥብ በአሁኑ ወቅት በአገራችን መሬት በግል ባለሃብትነት ሊያዝ የሚችልበት ሁኔታ ስለተቀየረ ብፍ/ሕግ ቁጥር 1172-1180 ላይ የተደነገጉትን የተፈፃሚነታቸው ጉዳይ ምን ያህል ነው የሚለውን ጉዳይ አጠያቂ ሆነዋል።
ከዚህ ነጥብ ጋር በተያያዘ ያለው ልምድ አመላካች የሆኑ ሁለት የፍ/ቤት ጉዳዮች ቀርቧል፦
ሀ) የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሰበር ችሎት በአመልካች አቶ ብርሃነ ገረመ እና በተጠሪዎች እነ ተወልደ ገረመ የነበረ ክርክር በሰበር መ/ቁ.16031 የካቲት 22/1997 ዓ/ም የሚከተለውን-ውሳኔ ሰጥቷል።
ጉዳዩ የተጀመረበት በትግራይ ማእኸላዊ ዞን ማእኸላይ ፍርድ ቤት የአሁን አመልካች በአድዋ ከተማ ቀበሌ 08 ውስጥ ስፋቱ 173.04 በሆነ በ1ኛ ተጠሪ ስም በተመራ ቦታ ላይ የተሰራውን ቤት ግምት ብር 110,000.00/አንድ መቶ አስር ሺ ብር/ ሌሎች ወጪዎች ተጨምሮ ሊከፈለኝ ይገባል በማለተ በአሁን ተጠሪዎች ላይ ክስ ይመስርታል። የግራ ቀኝ ክርክር እና ማስረጃቸውን ከሰማ በኃላ ቤቱን የሰራው ከሳሽ /አመልካች/ መሆኑን በምስክሮች የተረጋገጠ በመሆኑና ተከሳሾቹም መስራቱን አለመቃወማቸውን ስለተረዳን በሚል በፍ/ብ/ሕግ ቁ. 1180(2) መሰረት ተከሳሾቹ የግምቱን ሩብ ብር 27,500.00 እና ሌሎች ወጪዎች ጭምር ለከሳሹ ይክፈሉት ሲል ወሰነ። የትግራይ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ ሰሚና ሰበር ሰሚ ችሎቶችም የቀረበላቸው አቤቱታ ውድቅ ያረጉታል።
በመቀጠልም አመልካች ውሳኔው መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት የተፈፀመበት ነው በማለት ለፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ችሎት አቤቱታውን አቀረበ። የቅሬታው ዋናው ነጥብ ቤቱን የሰራሁት በተጠሪዎች ስምምነት ስለሆነ የካሳው መጠን በፍ/ስ/ሕግ ቁ. 1179 እና 1180 መሰረት ሊሰላ አይገባም፣ ቤቱን ለመስራት ያወጣሁት ብር 110,000.00 ሲሆን ይህንንም ተጠሪዎች አልተቃወሙትምና ቤቱን ከወሰዱት ግምቱን በሙሉ ሊከፍሉኝ ይገባል የሚል ነው ። ተጠሪዎችም የግምቱን ¼ኛ እንድንከፍል በመወሰኑ የተጎዳነው እኛ እንጂ እርሱ አይደለም ብለው ይከራከራሉ።
ሰበር ችሎትም አመልካች ግምትን ላገኝ ይገባኛል የሚለውን ቤት የሰራው እርሱ መሆኑ በስር ፍ/ቤቶች ተረጋግጧል። በሌላ በኩል ግን ተጠሪዎች መሬቱን የተመሩ ባለይዞታዎች እንጂ የመሬቱ ባለቤቶች አይደሉም። መሬት የመንግስት ሃብት መሆኑ ግልፅ ሆኖ ሳለም የይዞታ መብት ብቻ ያላቸውን ተጠሪዎች እንደመሬት ባለቤት መቁጠርና ጉዳዩን ከፍ ሲል ከተጠቀሱት የፍ/ብ/ሕጉ ድንጋጌዎች አንፃር መርምሮ ዳኝነት መስጠት የሚቻል እንዳልሆነ ያስቀምጣል።
ተጠሪዎች ቤቱን በሌላ ፍርድ ከአመልካች መረከባቸውን መዝገቡ እንደሚያስረዳ ገልፆ፤ አመልካች ቤቱን ለመስራት ብር 110,000.00 ማውጣቱ በስር ፍ/ቤቶች ተቀባይነት ማግኘቱን ከፍርዱ ይዘት መገንዘብ ይቻላል ካለ በኃላ አመልካቹ የጠየቀውን ግምት ብር 110,000.00 የማያገኝበት ሕጋዊ ምክንያት እንደሌለ በማስቀመጥ የስር ፍ/ቤቶች ውሳኔ በመሻር፤
1.ተጠሪዎች ለአመልካቹ ብር 110,000.00 ሊከፍሉት ይገባል፣
- 2.ተጠሪዎች የመጀመሪያውን አማራጭ ካልተቀበሉት ደግሞ በቦታው ላይ በአመልካቹ የተሰራውን ቤት እንዳለ ሊያስረክቡትና ሰመ ሃብቱንም በስሙ ሊያዞሩለት ይገባል ሲል ወስኗል።
አንድ ተንቀሳቃሽ ንብረት በሌላ ተንቀሳቃሽ ንብረት ላይ ሲጨመር የሚያመጣው ውጤት ሆኖ በሶሰት መንገዶች ይገለፃል።
1 በመለወጥ (Transformation or Specification) (ፍ/ሕግ ቁ. 1182)
አንድ ሰው የራሱ ጉልበት አና እንዲሁም በቅን ልቦና የሌላ ሰው ተንቀሳቃሽ ንብረት ተጠቅሞ ሌላ አዲስ ነገር የሰራ እንደሆነ የሚከሰት ነው። የዚህ አዲስ ነገር ወይም የተለወጠው ነገር ባለቤት ማን ሊሆን ይገባል የሚለው ጥያቄ መነሳቱ አይቀሬ ነው። የዚህ ጥያቄ መልስ በሁኔታ ላይ የተመሰረተ ነው። ይኸውም የጉልበቱ ዋጋ ከተሰራው /ከታደሰው/ ነገር ዋጋ የበለጠ እንደሆነ የተሰራው አዲስ ነገር ወይም የተለወጠው ነገር ጉልበቱን አፍስሶ ለስራው ወይም ለለወጠው ሰው ይሆናል። የታደሰው ንብረት ዋጋ የሚበልጥ ከሆነ ደግሞ የተሰራው ወይም የታደሰው ነገር ለባለ ንብረቱ ይሆናል። የስራው ግምት እና የታደሰው ነገር ዋጋ እኩል በሚሆንበት ጊዜስ የተሰራው /የታደሰው/ ነገር ለማን መሆን አለበት የሚለውን ጥያቄ ግን መልስ አይሰጥም።
በአጠቃላይ በዚህ ነጥብ ስር ላይ ግምት ውስጥ መግባት ያለባቸው መመዘኛዎች፦
- ስራው አዲስ ነገር የፈጠረ መሆን አለበት
- ስራውን የሰራው ሰው በቅን ልቦና ያደረገው መሆን አለበት
- በስራው ላይ የዋለ የጉልበት ዋጋ ከታደሰው/ከተለወጠው/ነገር ዋጋ የበለጠ መሆን አለበት። እነዚህ ሁኔታዎች ከተማሉ የተሰራው (የታደሰው ወይም የተለወጠው) ነገር ጉልበቱንና ዕውቀቱን ተጠቅሞ ለስራው (ለለወጠው) ሰው ይሆናል።
የሌላ ሃብት የሆነ ተንቀሳቃሽ ንብረት ተጠቅመው አዲስ ነገር ሊሰሩ የሚችሉ ሰዎች ለምሳሌ፦ ስኣሊዎች፣ ሸማኔዎች፣ ወርቅ ሰሪዎች፣ ልብስ ሰፊዎች፣ ሓወልት ሰሪዎች (የሚቀርፁ) ፣ ዳቦ ጋጋሪዎች፣ ምግብ ኣብሳዮች የመሳሰሉት ናቸው።
2 መቀላቀል (መወሃድ) (merger or Confusion) (ፍ/ሕግ ቁ.1183(1))
መቀላቀል ማለት የተለያዩ ሰዎች ንብረት የሆኑትን ሁለት ወይም ከዛ በላይ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች አንድ ላይ ሲቀላቀሉ ወይም ሲወሃዱ የሚከሰት ሆኖ በጣም ሳይጐዱ ወይም ሳይበላሹ ወይም በከባድ ስራ ወይም በብዙ ኪሳራ ካልሆነ በስተቀር ሊለያዩ ወይም ሊላቀቁ የማይችሉ እስከመሆን የተቀላቀሉ ወይም የተጣበቁ እንደሆነ ነው። የእነዚህ ነገሮች ቅልቅል ውጤት የሆነው ነገር የእነዛ ሰዎች እንደየድርሻቸው የጋራ ሃብት ይሆናል።
3 ሙሉ ክፍል መሆን (Embodiment/Adjunction) (ፍ/ሕግ ቁ.1183(2))
ሙሉ ክፍል መሆን (መቀላቀል) ማለት የተለያዩ ሰዎች ሃብት የሆኑትን ተንቀሳቃሽ ንብረቶች አንድ ላይ ሲጣመሩ (ሲቀላቀሉ) የሚያመለክት ሆኖ እያንዳንዳቸው ለመለየት የሚቻል ቢሆንም /ቅልቅላቸው ውህደት ስላልሆነ/ አንዱ ንብረት እንደ ዋና ሌላኛው እንደ ሙሉ ክፍል (intrinsic element) የሚታዩበት ሁኔታ ስለሚፈጠር የዋናው ነገር ባለቤት የሙሉ ክፍሉም ባለቤት ይሆናል።
መ/ ፍሬ (Fruits)
ፍሬ ሲባል ዋና ነገር /ንብረት/ እንዳለ ሆኖ በዚሁ ላይ ሌላ ፍሬ ሲጨመር ነው። በዚሁ ሁኔታ ተጨማሪው /ፍሬው/ ከዋናው ነገር ተለይቶ ሲወጣ ወይም ከእሱ ጋር ሲደመር የሚገኝ ነው። በዚህ ስር ሊካተቱ የሚችሉትን ሁለት ነገሮች ናቸው።
1 በተፈጥሮ የሚገኙ ፍሬዎች፦ የእንስሳት ውላጅ፣ የአትክልት ፍሬ የመሳሰሉት ሲሆኑ የእንስሳቱ ባለቤት የውላጅም ባለቤት ይሆናል። የአትክልቱ ባለቤት የፍሬ‘ውም ባለቤት ይሆናል።
2 ሰው ሰራሽ ፍሬዎች፦ ሰው ሰራሽ (Artificial) ፍሬዎች የምንላቸው በሁለት ሊከፈሉ የሚችሉ ሆኖው ሲቪል እና ኢንዳስትሪያል ይባላሉ። ሲቪል የምንላቸው ሰዎች በመካከላቸው በሚያደርጉት ውል/ስምምነት መሰረት የሚገኝ ነው። ለምሳሌ ፦ከቤቶች ክራይ የሚሰበሰብ ገንዘብ የቤቱ ባለቤት ሃብት ይሆናል። የገንዘብ ወለድም እንዲሁ የዋና ገንዘብ ባለቤት ሃብት ይሆናል። ኢንዳስትሪያል ፍሬዎች የምንላቸው ደግሞ መሬትን በማልማት የሚገኙ ፍሬዎች ናቸው።
- Details
- Category: Property Law
- Hits: 7989
በመርህ ደረጃ ሲታይ አንድ ንብረት ተቀባይ የሆነ ሰው ንብረቱ ከሚያስተላልፍለት ሌላ ሰው የበለጠ መብት አይኖረውም። አንድ ሰው ራሱ የባለሃብትነት መብት ሳይኖረው ማንኛውም የንብረት መብት ለሌላ ሰው ማስተላለፍ እንደማይችል ነው።
ንብረቱን የሚያስተላልፈው ሰው በባለሃብትነት መብቱ ላይ ጉድለት ያለበት እንደሆነ ያ ጉድለት ከንብረቱ ጋር አብሮ ወደ ተቀባዩ ይተላለፋል። በቅን ልቦና ባለይዞታ መሆን ባለሃብት ለመሆን ከሚያስችሉ መንገዶች (modalities) አንዱ ሆኖ ግዙፍነት ባላቸው መደበኛ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች ላይ ተፈፃሚነት የሚኖረውና ለሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች መብትና ግዴታ በሚሰጥና በሚያሽክም ውል (contract of sale of the thing under consideration) የሚገኝ ነው። ንብረቱ በቅን ልቦና የገዛ ሰው ሽያጩ ያ ንብረት ለመሸጥና ለማስተላለፍ የሚያስችል ሕጋዊ መብት እንዳለው ኣምኖ የገዛው መሆን አለበት። እዚህ ላይ ሕጉ ሁለት ተፋላሚ ጥቅሞችን (conflicting interests) ለማስማማት ወይም ሚዛናቸውን ለመጠበቅ ይሞክራል። ይኸውም፤ የቀድሞው የንብረቱ ባለሃብትና የንግዱ እንቅስቃሴ /የሶሰተኛ ወገን ጥቅም/ ናቸው። በአንድ በኩል የቀድሞው ባለሃብት ብዙ ደካም፣ ጥሮግሮ ያፈራውን ንብረት ያለአግባብ እንዳይነጠቅ ጥበቃ የሰጠው ሲሆን፤ በሌላ በኩል ደግሞ በቅን ልቦና ዕቃ የገዙ ሰዎች ዕቃው ከማይመለከተው ሰው ነው የገዛችሁት የተባሉ እነሱ በማያውቁት ጉዳይ ችግር ላይ እንዳይወድቁና በዚህ ሰበብም ነፃ የንግድ እንቅስቃሴው እንዳይገታ ለማድረግ ነው።
ከላይ እንደተመለከተው ይህ በቅን ልቦና ባለይዞታ በመሆን የባለሃብትነት መብት የማግኘት ጉዳይ ተፈፃሚነት የሚኖረው በመደበኛ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች (ordinary corporeal chattels) ላይ ነው። መርሁ ሙሉ በሙሉ ተፈፃሚ ሊሆን የማይችለው፤
- 1.በማይንቀሳቀሱ ንብረቶች ላይ
- 2.በልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች ላይ
- 3.ለህዝብ ጥቅም ተብለው በሚመደቡ ንብረቶች ላይ ነው (ፍ/ሕግ ቁ.1455)
በተንቀሳቃሽ ንብረት ላይም መርሁ ተፈፃሚ የሚሆንበትና የማይሆንበት ሁኔታ አሉ።
1.ተፈፃሚ የማይሆንበት ሁኔታ፤ የንብረቱ ባለሃብት በፍላጐቱና በፈቃዱ ለሌላ ሰው ያስተላለፈው እንደሆነና ተቀባዩም ወደ ሶሰተኛ ወገን በውል ያስተላለፈው እንደሆነ ኃላ የቀድሞው የንብረቱ ባለብት ከሶሰተኛው ወገን የመጠየቅ መብት አይኖረውም። ይህ ነገር ተቀባይ የሆነ ሰው ንብረቱ ካስተላለፈለት ሰው የበለጠ መብት የለውም ( “Nemo dat quod non habet,” “No one can transfer what he himself doesn’t have”)ለሚለው መርህ ልዩ ሁኔታ ነው። እዚህ ላይ የሚሰራ ወይም ተፈፃሚነት ያለው መርህ መብትህን /ንብረትህን/ በእምነት ከሰጠኸው ሰዉ ጠይቅ (“where you have put your faith there you must seek”) የሚለውን ነው። ስለዚ የንብረቱ የቀድሞ ባለሃብት መብቱን መጠየቅ ያለበት ከሰጠው ሰው እንጂ ከሶሰተኛው ወገን ሊሆን አይገባውም ማለት ነው። ለምሳሌ፦ በመያዣ (pledge) የተቀበለው፣ በብድር የወሰደው ንብረት ወደ ሶሰተኛ ወገን /በቅን ልቦና የገዛ/ ያስተላለፈው እንደሆነ ሶሰተኛው ወገን የባለሃብትነት መብት ያገኛል።
በቅን ልቦና ባለይዞታ በመሆን የአንድ ነገር ባለሃብት ለመሆን መሟላት ያለባቸው ሁኔታዎች አሉ።
ሀ/ በሻጭና በገዢ መካከል በተደረገ የሽያጭ ውል መሰረተ የተላለፈ ንብረት መሆን አለበት፣ ይኸውም ለሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች መብት የሚሰጥና ግዴተ የሚያሸክም መሆን አለበት፣ በሌላ ኣገላለፅ በስጦታ የተገኘን ንብረት በቅን ልቦና በመያዝ ባለሃብት መሆን እንደማይቻል ነው።
ለ/ በቅን ልቦና ባለይዞታ የሆነው ወደ ውሉ ሲገባ ለውሉ ምክንያት የሆነውን ንብረት ባለሃብት ለመሆን ኣስቦ ያደረገው መሆን አለበት።
ሐ/ ቅን ልቦናው ንብረቱን እጅ በሚያደርግበት ጊዜ መኖር አለበት።
መ/ ገዢው ንብረቱን ሲገዛ ከቅን ልቦ የተነሳ ከእውነተኛው ባለሃብት ነው ንብረቱ እየገዛሁት ያለሁት የሚል እምነት የነበረው መሆን አለበት፣
ሠ/ ገዢው የገዛው ንብረት ሲተላለፍለት ወይም እጅ በሚያደርግበት ጊዜ ቅን ልቦና የነበረው መሆን አለበት፣
ረ/ በቅን ልቦና የሚገዛው ንብረት መደበኛ ተንቀሳቓሽ ንብረት መሆን አለበት።
2.አንድ ሰው የሌላውን ሃብት /ነገር/ ለሌላ ሰው ማስተላለፍ አይችልም የሚል መርህ ተፈፃሚ የሚሆንበት ሁኔታ ፤ ንብረቱ ከባለቤቱ እጅ ሊወጣ የቻለው ከእርሱ ፍላጐትና ፈቃድ ውጭ የሆነ እንደሆነና ተቀባዩም ወደ ሶሰተኛ ወገን ያስተላለፈው እንደሆነ የቀድሞው ባለቤት በሕግ የተደነገገን የይርጋ ጊዜ ከማለፉ አስቀድሞ ንብረቴን መልስልኝ ብሎ ሶሰተኛ ወገንን ለመጠየቅ ይችላል። የዚህ ልዩ ሁኔታ በፍ/ሕግ ቁ.1167 ላይ የተደነገገውን ነው። ይህ የሕግ ድንጋጌ ጥሬ ገንዘብንና ላምጪው የሚከፈል ሰነድ የሚመለከት ሆኖ እንደ ልዩ ሁኔታ (exception) የተቀመጠበት ምኽንያት ደግሞ ገንዘብ ተመሳሳይና መለያ የሌለው /ከቁጥር በስተቀር/ በመሆኑና እንደ አጠቃላይ የመገበያያ መንገዲ (means of exchange) መጠን ነፃ ዝውውራቸው (free circulation) ጠብቀው እንዲያገለግሉ ሕጉ ጥበቃ ያደረገላቸው መሆኑን እንገነዘባለን። ከጥሬ ገንዘብና የገንዘብ ሰነዶች ውጭ ያሉትን የተሰረቁ ዕቃዎችን በተመለከተ ግን ሕጉ የባለሃበትነት መብት እንዳይደፈርና አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ከፍተኛ ጥበቃ ያደረገለት መሆኑን ነው። በቅን ልቦና የተሰረቀ ንብረት የገዛ ሰው ንብረቱ ለቀድሞው ባለሃብት የመመለስ ሕጋዊ ግዴታ ያለበት ቢሆንም ለዚህ ንብረት ያወጣውን ገንዘብ ከሸጠለት ሰው የመጠየቅ መብት እንዳለውም ሕጉ አስቀምጧል። በመብቱ መጠቀም የሚችለው ግን ንብረቱ /ዕቃው/ የገዛው በንግድ ቤት፣ በህዝብ ገበያ ውስጥ ወይም ዕቃ በሓራጅ በሚሸጥበት አደባባይ ውስጥ የሆነ እንደሆነ ነው። በሌላ በኩል የፍ/ሕጉ የፈረንሳኛው ቅጂ ግን የተሰረቀ ንብረት በቅን ልቦና የገዛ ሰው ገንዘቡ ማስመለስ ያለበት ከንብረቱ ባለቤት እንደሆነ ነው የሚደነግገው።
- Details
- Category: Property Law
- Hits: 7007
ሃብትነት ከሁሉም ከንብረት ጋር ተያያዥነት ካላቸው መብቶች አንፃር ሲታይ ከፍተኛው ቦታ የያዘ መብት ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም።
ሃብት እንዴት እንደሚገኝ፣ እንደሚተላለፍ፣ እንደሚቀርና እንደሚረጋገጥ ከማየታችን በፊት የሃብት ትርጉም ምን እንደሆነ ማየቱ ተገቢነት ስለሚኖረው በአጭሩ እንደሚከተለው ቀርቧል። የፍትሐብሄር ሕጋችን በምዕራፍ ሁለት ክፍል አንድ ላይ “ሃብትነት ማለት በአንድ ግዙፍ ንብረት ከሁሉ የሰፋ መብትን የያዘ ማለት ነው” በሚል መልኩ ተገልፆ ይገኛል። ቢሆንም የድንጋጌው አባባል ትርጉም ነው ብሎ ማስቀመጥ የሚያስደፍር አይደለም። ትርጉም ነው ሊባል አይችልም ብቻ ሳይሆን ንብረትን የሚገልፁ ነገሮችን በበቂ ሁኔታ ተገልፆአል ለማለትም ያስቸግራል። ምክንያቱም ይህ መብት እንዴት ሰፊ ሊሆን ቻለ የሚል ጥያቄ እንኳ የመለሰ አይደለም። በተጨማሪ በአንድ ግዙፍ ንብረት ላይ (corporeal things) የሚኖርን መብት ብቻ አስቀመጠ እንጂ ግዙፋዊ ህልውና ስለሌላቸው (incorporeal things) በተመለከተ ሳያካትት ቀርተዋል:: ሃብትነት ከሁሉም የሰፋ መብት ነው ሲባል ግን ከይዞታ፣ ከአለባ እና ከንብረት አገልግሎት መብቶች አንፃር ሲታይ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል።
ባለሃብትነት ማለት ማንም ሰው በንብረቱ ላይ የሚኖረው የመጠቀም (usus) ፣ ፍሬው የመሰብሰብ (fructus) እና የባለሃብትነት መብት ለሌላ ሰው የማስተላለፍ (abusus) መብት ነው። እዚህ ላይ abusus ማለት በኑዛዜ ወይም በውል ለሌላ ሰው ማስተላለፍ፣ አይጠቅመኝም ብሎ መጣል የሚያጠቃልል ፅንብ ሓሳብ ነው።
ባለሃብትነት ከሁሉም በላይ የሰፋ መብት ነው ሲባል ግን ምንም በሕግ የተቀመጠ ገደብ (restriction) የለውም ማለት አይደለም። ማንኛውም ባለሃብት የሌሎች ግለሰቦች ወይም የህዝብ መብትና ፍላጎት በሚፃረር መልኩ መብቱን ሊጠቀምበት ይችላል ማለት አይደለም። የባለሃብትነት መብት ከሁሉም በላይ የሰፋ መብት ቢሆንም የሌሎች መብት እስካልተቃረነ ድረስ የሚጠቀምበት ስለሚሆን ገደብ የተበጀለት መብት ነው ። (ፍ/ሕግ ቁ.1204(1) እና 1205(1)ይመለከተዋል)
ባለሃብትነት በተለይ የግል ባለሃብትነት በተመለከተ በተለያዩ ሙሁራን፣ ፈላስፋዎች እና የኢኮኖሚ ሙሁራን መካከል ሲያከራክር የቆየ ነው። የግል ባለሃብትነት የሚባል ነገር መኖር የለበትም የሚሉ ወገኖች የሚያቀርቡት ምክንያት ፤ አንዳንዶቹ እንደሚሉት አንድ ሰው በሌላ ሰው ላይ ብዝበዛ እንዲያደርግ ሊፈቀድለት አይገባም። ሌሎች እንደሚሉትም ሰዎች በመካከላቸው በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ግንኙነት እንዳይኖራቸው የሚያደርግ ነው። ወደ የኢኮኖሚ አናርክነት ሊያመራም ይችላል ይላሉ።
የግል ባለሃብትነት የሚደግፉ ወገኖች የሚያቀርቡት አስተያየት ደግሞ፤ የግል ባለሃብትነት የማንደግፍ ከሆነ ስለግለሰቦች መናገር ትርጉም አይኖረውም። የባለሃብትነት መብት ተፈጥሮኣዊ መብት እና የኢኮኖሚ እድገት መሳሪያ ነው፣ ለግለሰቦች ነፃነት ዋስትና የሚሰጥ ነው። የጋራ እድገት ለማሳካትም ቢሆን የግል ሃብት የሕግ ጥበቃ በስተቀር ሳያገኝ ሊታሰብ አይችልም ይላሉ። ይህ ሓሳብ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተነቐባይነት ያገኘና እንደ ተፈጥሮአዊ መብት ተደርጎ የተወሰደበት ሁኔታ ነው ያለው። ሕገ መንግስታችንም ከፍተኛ ግምት እንደሰጠው ነው መገንዘብ የሚቻለው።
ሃብት ስለሚገኝበት ሁኔታ፣ ሃብትን ስለማስተላለፍ፣ ሃብት ስለሚቀርበትና ስለ ሃብትነት ማስረጃ
1 ሃብት ስለሚገኝበት ሁኔታ
ሃብት ማግኘት ማለት አንድ ሰው ያለምንም ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ የንብረቱ ባለቤት የሚሆንበት፣ ሕግና ስርዓት በሚፈቅደው መሰረት በእጁ የሚያስገባበት ሁኔታ የሚገልፅ ሆኖ ሕግ ራሱ የባለቤትነት ደረጃ (status) የሚሰጠው ነው። በዚህ መሰረት የተለያዩ የሃብት ማግኛ መንገዶች ኣሉ። እነዚህ የሃብት ማግኛ መንገዶች እንደሚከተለው ለማየት እንሞክራለን።
ሀ) ባለቤት የሌላቸው ንብረቶች በመያዝ ባለሃብት ስለመሆን(0ccupation)
አንድ ባለቤት የሌለው ንብረት በመያዝ ባለሃብት የመሆን ጉዳይ ከሁሉም የሃብት ማግኛ መንገዶች በላይ ረዥም ዕድሜ ያለው ነው ብቻ ሳይሆን ከሌሎች የበለጠ የሃብት ማግኛ አግባብም ነው።
መያዝ ሲባል አንድ ባለቤት የሌለው ግዙፍነት ያለው ነገር /ንብረት/ የእዛ ነገር ባለቤት ለመሆን በማሰብ በቁጥጥር ስር ማድረግ ወይም መያዝ ማለት ነው። (ፍ/ሕግ ቁጥር 1151 ይመለከተዋል) ። አንድ ነገር በመያዝ ባለቤት ለመሆን አንዳንድ ቅድመ ሁኔታዎች መሟላት አለባቸው።
6. ንብረቱ ግዙፍነት ያለው ተንቀሳቃሽ ነገር መሆን አለበት
- 1.በግል ባለቤትነት ሊያዝ የሚችል መሆን አለበት
- 2.ንብረቱ ባለቤት የሌለው መሆን አለበት
- 3.የንብረቱ ባለሃብት ለመሆን ሓሳብ (intention) መኖር አለበት።
ንብረቱ ግዙፍነት ያለው ተንቀሳቃሽ ንብረት መሆን አለበት። በሌላ አባባል ግዙፍነት የሌላቸው ንብረቶች /ምሳሌ የፈጠራ ስራ/ ለመያዝ ከምዝገባ ውጭ ሊሆን ስለማይቻል ነው። የእነዚህ ንብረቶች ባለመብት ማን እንደሆነ በምዝገባ የሚታወቅ ሆኖ ምዝገባው የተሰረዘ እንደሆነ ግን መብቶቹ ትርጉም የለሽ የሚያደርጋቸው ስለሚሆን ነው። እንዲሁም ተንቀሳቃሽ ንብረት መሆን አለባቸው ሲባል የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን በመርህ ደረጃ መያዝ የሚቻለው በምዝገባና የባለቤትነት ደብተር በመያዝ ስለሆነ ነው።አንዳንድ የሚንቀሳቀሱ ንብረቶች በተለይ ልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች የሚባሉ እንደተሽከርካሪዎች፣ መርከብ፣ ኣውሮኘላን ወዘተ የመሳሰሉትን በመያዝ አማካኝነት የግል ሃብት ሊሆኑ የማይችሉ ናቸው። በተጨማሪም ለህዝብ ጥቅም ወይም አገልግሎት ተብለው የተመደቡ ተንቀሳቃሽ ንብረቶች ቢሆኑም በግል ሊያዙ አይችሉም (ፍ/ሕግ ቁ.1448 እና 1457)።
በመያዝ አማካኝነት ባለሃብት መሆን የሚቻልባቸው የተንቀሳቃሽ ንብረት ዓይነቶች እንደሚከተለው ማስቀመጥ ይቻላል።
- 1.ባለቤት የሌላቸው ነገሮች (Master less things)
- 2.የተቀበረ ገንዘብ (Treasure)
- 3.የጠፋ ንብረት (lost things)
- 4.የተተው ነገሮች (abandoned things)
- 5.ከጠላት የተገኘ ንብረት (Seizure of Enemy property)
- 1)ባለሃብት የሌላቸው ነገሮች የምንላቸው፤ ባለቤት ኖሮአቸው የማያውቁ ነገሮች ሆኖው ለመጀመርያ ጊዜ በባለቤትነት የተያዙ ናቸው። እንዲሁም ከመያዛቸው በፊት በባለቤትነት ስር የነበሩ ቢሆኑም ኃላ በባለቤቱ የተጣሉ ንብረቶች ናቸው። የተጣሉ ነገሮች ናቸው የሚባሉት የቀድሞ ባለቤታቸው የይመለስልኝ አቤቱታ ሊያቀርብባቸው የማይችሉ ናቸው።
እንስሳትና ንብ (ፍ/ሕግ ቁ.1152-1153)
እንስሳት ስንል ለማዳ እንስሳት ኖሮው በኃላ የጠፉ ወይም በባለቤትነት ስር ገብተው የማያውቁ የዱር አንስሳት ሊሆኑ ይችላሉ። ባለቤታቸው የጣላቸው /የተዋቸው/ ወይም ከባለቤታቸው እጅ የጠፉ እንስሳት የምንላቸው አንደ ከብት፣ ፍየልና በግ፣ የጋማ ከብቶች፣ ውሾች እና ሌሎች ለማዳ የነበሩ እንስሳት የሚያጠቃለል ነው። እንደ እነዚህ የመሳሰሉትን ለማዳ የነበሩና ኃላ የጠፉ ወይም የተጣሉ እንስሳት ባለቤት ለመሆን በሕግ የተቀመጠ የይርጋ ጊዜ ማለፍ ያስፈልጋል። የይርጋው ጊዜ ከማለፉ በፊት የቀድሞው ባለሃብት የእኔ ንብረት ነው ብሎ ንብረቱን ካገኘ /ከያዘ/ ሰው ከመጠየቅ የሚያግደው ነገር አይኖርም። በፍ/ሕግ ቁ.1152(1) ስር እንደተደነገገው ለማዳ የሆኑ ወይም የተያዙ እንስሳት ባለሃብት ከሆነው ሰው ቢያመልጡና ቢጠፉ ባለቤቱም በሚከተለው ወር ውስጥ ሳይፈለጋቸው የቀረ እንደሆነ ወይም አንድ ወር ሙሉ መፈለጉን ቢተው ባለቤት የሌላቸው ይሆናሉ። እነዚህ አምልጠው የጠፉ እንስሳት ሌላ ሰው ቢያገኛቸውና የተቀመጠው የአንድ ወር የይርጋ ጊዜ ቢያልፍ ይህ ሰው የእነዚህ ነገሮች ባለቤት ይሆናል። ቢሆንም ይህ የይርጋ ድንጋጌ ለቀንድ ከብቶች፣ ለጋማ ከብቶችና ለግመሎች ተፈፃሚ እንደማይሆን በቁጥር 1152(2) ተመልክቷል። ይህ ልዩነት የተፈጠረበት ምክንያት ለምንድነው? ውድ ለሆኑና ከፍተኛ ጠቀሜታ ላላቸው ንብረቶች/እንስሳት/አጭር የይርጋ ጊዜ ማስቀመጥ ፍትሓዊ ሊሆን አይችልም። ምክንያቱም አንድ ሰው ይህን የመሰሉ እንስሳት ጠፍተውበት ችላ ብሎ ይተዋቸዋል ተብሎም አይገመትምና ነው። የአንድ ወር የይርጋ ጊዜ አይመለከታቸውም ማለት ግን ፈፅሞ ይርጋ የላቸውም ማለት ነውን?
ከቀንድ ከብቶች፣ ከጋማ ከብቶች እና ከግመሎች ውጭ ያሉት እንስሳትን በተመለከተ የአንድ ወር የይርጋ ጊዜ ያስቀመጠበት ምክንያት ደግሞ ከሌሎች ጋር ሲወዳደሩ ውድ ካለ መሆናቸውና ከፍተኛ ጥቅም ይሰጣሉ ተብለው ስለማይገመት ባለቤታቸው ከአንድ ወር በላይ ጊዜ ለፍለጋቸው ያጠፋል ተብሎ ስለማይገመት ይመስላል።
የዱር እንስሳት ከሚባሉት ወፎች፣ ዓሳዎች፣ ንቦች ወዘተ መጥቀስ የሚቻል ሆኖ ባለቤት ያልነበራቸው ተብሎ ከሚጠሩ እንስሳት ጠቂቶቹ ናቸው። እነዚህ እንስሳት አብዛኛው ጊዜ በግል ባለሃብትነት እንዳይያዙ የተከለከሉ አይደሉም። ይሁን እንጂ እንደዚህ የመሳሰሉት እንስሳት ለመያዝ ወይም ለማደን፣ ዓሳ ለማጥመድ ወዘተ የአገሪቱ ሕግና ደንብ በሚፈቅደው መሰረት ሊፈፀም እንደሚገባው ግን መዘንጋት የለበትም ነው። ፈቃድ አስፈላጊ ከሆነም ከሚመለከተው ኣካል መጠየቅና ፈቃድ መያዝ ያስፈልጋል።
ንቦችን በተመለከተ በፍ/ሕግ ቁጥር 1153 ላይ የተደነገገ ሲሆን፤ ቆፎአቸውን ትተው የሄዱ ንቦች በቆፎአቸው ከወጡበት ቀን አንስቶ ባለቤት የሌላቸው ይሆናሉ፣ ወደ ሌላ ቆፎ የገቡ እንደሆነ የቆፎው ባለቤት የንቦችም ባለቤት ይሆናል፣ ንቦች ከቆፎአቸው ወጥተው በሚበሩበት ጊዜ የቀድሞው ባለቤት እየተከተላቸው የሄደ እንደሆነና ወደ ሌላ ቆፎ ሲገቡ የደረሰባቸው እንደሆነ መልሶ ሊወስዳቸው እንደሚችል ነው ከሕጉ መገንዘብ የሚቻለው።
ጠፍተው የተገኙ ነገሮች (ፍ/ሕግ ቁ.1154-1158)
አንድ ሰው በቸልተኝነት ወይም ከፍላጐቱ ውጭ በሆነ ሁኔታ ንብረቱ ከእጁ የጠፋ እንደሆነና ያ የጠፋው ንብረት ሌላ ሰው ያገኘው እንደሆነ ጠፍቶ የተገኘ ዕቃ (ነገር) ይባላል። ለምሳሌ፦ በዝናብ ሓይል፣ በጐርፍ፣ በንፋስ ወዘተ የተወሰደበት እንደሆነ፣ የንብረቱ ባለቤት የሆነ ቦታ ላይ ረስቶት የሄደ እንደሆነ፣ ንብረቱ በሌላ ሰው የተደበቀበት እንደሆነ፣ በእንስሳት የተወሰደበት እንደሆነ፣ ከሌላ ሰው ንብረት ጋር በመደባለቁ ምክንያት ሳያገኝ የቀረ እንደሆነ ወይም በሌላ ተመሳሳይ ምክንያት ንብረቱ የት እንዳለ ለማወቅ ያልቻለ እንደሆነ ነው። እንደዚህ ዓይነት ንብረት በአንድ ወይም በብዙ ሰዎች ሊገኝ ይችላል።
የጠፋ ንብረትና በማወቅ የተጣለ (የተተወ) ንብረት ልዩነት አላቸው። ይኸውም፤ የጠፋ ንብረት ሲሆን በሕግ የተቀመጠ የጊዜ ገደብ (ይርጋ) እስኪያልፍ ድረስ የቀድሞው ባለቤት (ባለሃብት) መብት እንደተጠበቀ ይቆያል። የጠፋ ንብረት በሚሆንበት ጊዜ ያ ንብረት ባገኘ ሰው ላይ ሕጉ ግዴታዎች አስቀምጧል፤ እንዲሁም መብቶቹም ደንግጓል።
የጠፋ ንብረት ያገኘ ሰው ግዴታዎች፦
- 1.የአስተዳደር ደንብ በሚያዘው መሰረት ለሚመለከተው የመንግስት አካል የጠፋ ንብረት ያገኘ ስለመሆኑ የማሳወቅ ግዴታ (ቁ.1154(1)) ።ይህንን ግዴታ ካልተወጣ በኢፌዴሪ ወንጀል ሕግ አንቀፅ ተጠያቂ ይሆናል።
- 2.ንብረት የጠፋበት ሰው ንብረቱ የተገኘ መሆኑንና መልሶ እንዲወስድ በማስታወቅያ የመንገር (ቁ.1154(2)) ግዴታ አለበት። ይህ ማስታወቀያ በመጋናኛ ብዙሃን በመንገር ወይም በገበያ ላይ በመግለፅ ወይም በሌላ መንገድ ሊፈፀም ይችላል። ሆኖም ግን በመጋናኛ ብዙሃን መንገር ብዙ ሲሰራበት የማይታይ ከመሆኑም በላይ ከወጪ አንፃር ሲታይም ውድ ሊሆን ይችላል። ሌላ የማሳወቅያ መንገድም ቢሆን ብዙ ሲሰራበት አይሰተዋልም።
- 3.ያገኘውን ንብረት ለመጠበቅ ተገቢ ጥንቃቄ ማደረግ ይጠበቅበታል (ቁ.1155(2))። የጠፋ ንብረት ያገኘ ሰው ንብረቱ እንዳይሰረቅ ወይም እንዳይበላሽ እንደራሱ ንብረት እንክብካቤ ሊያደርግለት ይገባል። ከአቅም በላይ በሆነ ምክንያት ንብረቱ ጉዳት የደረሰበት ወይም የተበላሸ እንደሆነ ግን ተጠያቂ አይሆንም።
የጠፋ ንብረት ያገኘ ሰው መብቶች፦
ሀ/ የንብረቱ ባለቤት እስኪመጣ ድረስ በእጁ አድርጎ የማስቀመጥ (ቁ.1155 (1))
ለ/ ጠፍቶ የተገኘው ንብረት ሊበላሽ ወይም ሊበሰብስ፣ ሊያረጅ የሚችል ወዘተ ወይም ለጥበቃው ብዙ ወጪ የሚጠይቅ ከሆነ ግልፅ በሆነ ቦታ ላይ በሓራጅ የመሸጥ (ቁ.1156 (1)) ። ለብዙ ወጪ የሚዳርግ ከሆነ የሚለውን አባባል ከንብረቱ ዋጋ በማወዳደር የሚታይ ነው።
ሐ/ ከንብረቱ ባለቤት አንድ አራተኛው የንብረቱ ዋጋ በጉርሻ መልክ እንደየሁኔታው ሊያገኝ
ይችላል። እዚህ ላይ ጉርሻው የመስጠት ወይም ያለመስጠት ስልጣን ለዳኞች የተሰጠ ነው
(ቁ.1158 (1)) ። የጉርሻው መጠን ሊወሰን የሚችለው ንብረቱ ያገኘውን ሰው እና የንብረቱ ባለቤት ያላቸው ሃብትና እንዲሁም የንብረቱ ባለቤት የጠፋውን ንብረት ፈልጎ ለማግኘት የነበረው ዕድል መጥበብና መስፋት ታሳቢ ያደረገ ነው።
መ/ለንብረቱ ጥበቃ ወይም ለሽያጭ ፣ የንብረቱ ባለቤት ቀርቦ ንብረቱን እንዲረከብ ለማስታወቅ ያወጣውን ወጪ እንዲተካለት የመጠየቅ መብት (ቁ.1157(2))። የንብረቱ ባለቤት የሆነ ሰው ላግኚው ወጪዎቹ እስካልተካለት ድረስ ንብረቱን በዕዳ ይዞ የማቆየት መብት አለው።
ሰ/ የይርጋ ጊዜው ያለፈ እንደሆነ የጠፋውን ንብረት ባለቤት የመሆን (ቁ.1157(1))። ይህ መብት ከፍ/ሕግ ቁጥር 1192 ጋር ተያይዞ የሚታይ ነው።
የተጣሉ ወይም የተተው ነገሮች /ንብረቶች/ ከጠፉ ንብረቶች ልዩነት እንዳላቸው ግንዛቤ መውሰድ ያስፈልጋል። ንብረቶች ከባለቤታቸው ፈቃድ ውጭ፤ ማለትም ከቸልተኝነት የተነሳ ወይም ከዓቅም በላይ በሆነ ሁኔታ ሊጠፉ እነደሚችሉ ከላይ ተመልክተናል። የተጣሉ ወይም የተተው ንብረቶች ግን የእነዚህ ንብረቶች ባለቤት በማወቅ ከአሁን በኃላ አይጠቅሙኝም ብሎ የጣላቸው ወይም የተዋቸው ናቸው። ስለሆነም የቀድሞው ባለቤት የባለሃበትነት መብቱ ንብረቶቹን እንደጣላቸው ወዲያውኑ ይቋርጣል። እነዚህ ነገሮች እንደተጣሉ ወዲያውኑ ሌላ ሰው ያገኛቸው ወይም ያነሳቸው እንደሆነ ያ ሰው ካገኛቸው /ካነሳቸው/ ጊዜ ጀምሮ የእነዚህ ነገሮች ባለሃብት ይሆናል። ስለዚህ እዚህ ላይ እንደ ዋና ነጥብ ተደርጎ የሚወስደው የቀድመው ባለሃበት ንብረቱ ከእጁ ሊወጣ የቻለው በራሱ ፈቃድ ነው ወይስ አይደለም የሚል ይሆናል።
ስለተቀበረ ገንዘብ (Treasure) (ፍ/ሕግ ቁ.1159-1160)
የተቀበረ ገንዘብ የሚባለው ቀደም ሲል ባለቤት የነበረው ነው ተብሎ የሚታመን ሆኖ ኃላ ግን አንድ ቦታ ላይ እንደተቀበረ ተረስቶ የቀረ ነው ብሎ ማስቀመጥ ይቻላል። ይህ ድንጋጌ ተጠፍቶ የተገኘ ንብረት የሚመለከቱ ድንጋጌዎችን ልዩ ሁኔታ (exception) ነው ማለት ይቻላል። አንድ ነገር የተቀበረ ገንዘብ ነወ ብሎ ለመሰየም፦
- 1.ተቀብሮ የተገኘው ንብረት ተንቀሳቃሽ ንብረት መሆን አለበት፣
- 2.በሚንቀሳቀስ ወይም በማይንቀሳቀስ ንብረት ውስጥ ተቀብሮ የቆየ ነገር መሆን አለበት፣
- 3.የራሱ ነፃ ህልውና ኖሮት ተቀብሮ ከተገኘበት ንብረት ጋር በቀላሉ ሊለያይ የሚችል መሆን አለበት፣ ከመያዣው ሊለያይ የማይችል ከሆነ የእዛ መያዣ ሙሉ ኣካል /ክፍል/ እንደሆነ ተደርጎ ስለሚቆጠር ነው።
- 4.ቢያንስ ለ50/ሃምሳ/ ዓመታት ያህል ተቀብሮ የነበረ መሆን አለበት
- 5.ገንዘቡ ሲገኝ ባለቤት ያልነበረው ወይም የእኔ ነው ብሎ አሳማኝ ነገር ሊያቀርብበት የማይችል መሆን አለበት።
ከዚህ ጋር ተያይዞ መነሳት ያለበት ጥያቄ ተቀብሮ የተገኘውን ገንዘብ ባለቤት የሚሆነው ማን ነው የሚልው ነው። ይህ ጥያቄ ለመመለስ ሁለት ሁኔታዎችን ግምት ውስጥ ማስገባት ያስፈልጋል። ይኸውም፤ የተቀበረውን ገንዘብ ያገኘ ሰው የመያዥውም ባለቤት የሆነ እንደሆነ ገንዘቡም የራሱ ይሆናል። የተቀበረው ገንዘብ ያገኘ ሰው የመያዣው ባለቤት ካልሆነ ደግሞ ሁለት ሁኔታዎች ይኖራሉ። አንደኛው ገንዘቡ ሊያገኘው የቻለው በራሱ ጥረት ወይም በአጋጣሚ የሆነ እንደሆነ የተገኘውን ገንዘብ /ንብረት/ ግማሹ በጉርሻ መልክ ለራሱ ግማሹ ደግሞ ለመያዣው ባለቤት ይሆናል። ሁለተኛ ንብረቱ ሊያገኝ የቻለው በመያዣው ባለቤት ትእዛዝ የሆነ አንደሆነ ግን የጉልበቱ ዋጋ ያገኝ እንደሆነ እንጂ ከተገኘው ገንዘብ/ንብረት/ ተካፋይ ሊሆን አይችልም።
እዚህ ላይ ግልፅ መሆን ያለበት ነገር ቢኖር አንቲካ የሚባሉ ጥንታዊ ዕቃዎች ፤ ለምሳሌ በአርኪዮሎጂ ቁፈራ የሚገኙትን ነገሮች እንደተቀበረ ንብረት እንደማይቆጠሩና ለእነሱ መተዳደርያ ተብለው በሚወጡ ልዩ ሕጎች/ደንቦች እንደሚመሩ ነው።
ስለ ጥንታዊ ታሪካዊ ቅርሶች የሚደነግገውን ኣዋጅ ቁጥር 229/1958 በአንቀፅ 2/ሀ/ ስር የተመለከተ ሲሆን “ጥንታዊ ቅርስ ማለት ከ1850 ዓ/ም በፊት የተሰራ ማናቸውም ዓይነት ሰው ሰራሽ ስራ ወይም ዕቃ ማለት ነው” በሚል መልኩ አስቀምጦታል። የእነዚህ ንብረቶች ባለቤት መንግስት ወይም የአገሪቱ ሃብቶቸ እንደሆኑና የሚንቀሳቀሱና የማይንቀሳቀሱ ንብረቶች እንደሚያጠቃልልም በዚሁ አዋጅ ዓነቀፅ 3 ላይ ተመልክቶ እንደነበር መገንዘብ ይቻላል። ጥንታዊ ቅርስ በእጁ ይዞ የሚገኝ ሰውም ከሚመለከተው የመንግስት አካል ፊት ቀረቦ ማስመዝገብ እንዳለበትና እስኪያስረክብ ድረስ ብቻ በእጁ ማቆየት እንደሚችል ነው ከአዋጁ አንቀፅ 4 መረዳት የሚቻለው:: ይህ አዋጅ ቁጥር 229/1958 በአዋጅ ቁጥር 36/1982 የተሻረ ሲሆን አዋጅ ቁጥር 36/1982 ደገሞ በአዋጅ ቁጥር 209/1992 ተሽረዋል::
በ1992 ዓ.ም ስለቅርስ ጥናትና አጠባበቅ የወጣ አዋጅ ቁጥር 209/1992 ቅርስን አስመለክቶ-የደነገገው ፍ/ሕጉ ካስቀመጠው ለየት ባለ መልኩ ነው::
ቅርስ የሚንቀሳቀስ ወይም የማይንቀሳቀስ ወይም ግዙፍነት ያለው ወይም የሌለው ነገር ሊሆን እንድሚችል በአዋጁ አንቀፅ 3 ስር የተካተተ ሲሆን፤ በአዋጁ ዓነቀፅ 14(1) ደግሞ ቅርሶቸ በመንግስት ወይም በማናቸውም ሰው ባለቤትነት ሊያዙ እንደሚችሉ ይገልፃል::
ይህ በእንዲህ እንዳለ ቅርስ ከሌላ ሃብት የሚለይበት ሁኔታዎቸ አሉት:: እነዚህም በግዴታ (duties) እና በገደብ (restriction) መልክ የተቀመጡ ናቸው::
የቅርስ ባለሃብት ግዴታዎች በተመለከተ በአዋጁ አንቀፅ 18 ላይ የተደነገጉ ሲሆን፤ ማናቸውም ቅርስ በባለቤትነት ያየዘ ሰው:
1. በራሱ ወጭ ለቅርሱ ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ ማድረግ
2. ቅርሱን ለኤግዚብሽን ወይም በሌላ ሁኔታ ለህዝብ እንዲታይ በባለስልጣን ሲጠየቅ መፍቀድ
3. ለቅርሱ አያያዝና አጠቃቀም የሚመለከቱ የዚህን አዋጅ ድንጋጌዎችና በአዋጁ መሰረት የወጡ ደንቦችና መመርያዎችን ማክበረ አለበት ይላል
እነዲሁም ማናቸውመ ሰው በባለቤትነት የያዘውን ቅርስ ሚኒስትሩ በሚያወጣው መመሪያ መሰረት የማስመዘገብ ግዴታ እንዳለበት (አንቀፅ 16(1))፤ የማይንቀሳቀስ ቅርስን እና የተመዘገበ ተንቀሳቃሽ ቅርስ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ለማንቀሳቀስ ፈቃድ እንደሚያስፈልገው ነው ከአዋጁ ይዘት ግንዛቤ መውሰድ የሚቻለው (አንቀፅ 21)::
ቅርሶች በመንግስት ብቻ ሳይሆን በማናቸውም ሰው በባለቤትነት ሊያዙ እንደሚችሉ አይተናል:: ይሁን እንጂ ይህ የቅርስ ባለቤትነት ለሌላ ሰው ለማስተላለፍ እንደ ሌላ የንብረት ዓይነት በባለ ይዞታው ወሳኔ ብቻ የሚፈፀም አይደለም:: በአዋጁ አንቀፅ 23 ላይ እንደተመለከተው፤ ማንኛውም ሰው የያዘውን ቅርስ በማናቸውም ሁኔታ ለሌላ ሰው ሲያሰተላልፍ ሁለቱም ወገኖች በቅድሚያ ባለስልጣኑን በፅሑፍ ማሳወቅ እንዳለባቸው እና ባለስልጣኑ ደግሞ ለሽያጭ የቀረቡ ቅርሶችን የመግዛተ ቅድሚያ መብት እንዳለው ተመልክተዋል::
ቅርሶችን በሽያጭ መልክ ለሌላ ሰው ማስተላለፍ እንደሚቻል አዋጁ ቢጠቁምም በሌላ መልኩ ደግሞ ለንግድ ዓላማ ሲባል መግዛትና መሸጥ እንደማይቻል በሕግ ተገድበዋል (አንቀፅ 24(1) ይመለከተዋል):: ይህ ብቻ ሳይሆን ተገቢ ጥበቃ፣ ጥገናና እድሳት ያልተደረገለት ወይም ለብልሽት የተጋለጠ ወዘተ ቅርስ ሲሆን፣ በቤተመዘክር ማስቀመጥ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እና ፈቃድ ሳያገኝ ወደ ውጭ አገር ሲወጣ የተገኘ እንደሆነም በመንግስት ሊወረስ እንደሚችል ነው(አንቀፅ 25):: በተጨማሪም በፍለጋ፣ ግኝትና ጥናት የተገኘ ቅርስ በአዋጁ (አንቀፅ 35(3)) መሰረት ለመንግስት እንድሚያስረክብ (አንቀፅ 29) እና ስለቅርስ ጥናት ያካሄደ ሰው የጥናቱ ውጤት የሆነውን ማናቸውንም ፅሑፍ በሚመለከት የባለሃብትነት መብት በፍ/ሕግ መሰረት እንደሆነ ተመለክተዋል(አንቀፅ 40):: እነዲሁም ማንኛውም ሰው የማኣድን፣ የህንፃ፤ የመንገድ ወይም ተመሳሳይ ስራ ለማካሄድ ባደረገው ቁፋሮ ወይም በማናቸወም አጋጣሚ ሁኔታ ቅርሶችን ያገኘ እንደሆነ ለሚመለከተው አካል ማሳወቅ ያለበት ሆኖ ሽልማት የማግኘት መብት እንዳለውም በአዋጁ ውስጥ ተካትተዋል (አንቀፅ 41 ይመለከተዋል)::
በአጣቃላይአዋጁ ሲታይ አንድ ሰው የቅርስ ባለቤት ሊሆነ እንደሚችል ቢደነግግም እንደሌላ ዓይነት ንብረት የፈለገው ነገር ሊያደረገው አይችልም:: ይህ የሆነበት ምከንያት ደግሞ በቅርስ ባለቤትነት ላይ በርከት ያሉ ግዴታዎች (duties) እና ገደቦቸ (restrictions) ያሉበት በመሆኑ ነው::
የጠላት ንብረት መያዝ (Seizure of enemy property)
የጠላት ንብረት በመያዝ ባለቤትነት /ባለሃብትነት/ ማረጋገጥ የሚቻለው ለውግያ /ጦርነት/ ተብሎ የተመደበውን ንብረት በሌላ ሓይል ወይም መንግስት ሲማረክ ወይም በቁጥጥር ስር ሲገባ ነው። ንብረቱ ከተማረከ በኃላ የማራኪው ሓይል ወይም መንግስት ንብረት ይሆናል። እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሲያጋጥም በዓለም አቀፍ ሕግና በፓብሊክ ሎዉ የሚመራ ይሆናል። በግለሰብ ደረጃም ሊያዝ የሚችል ነው ተብሎ አይታሰብም።
- Details
- Category: Property Law
- Hits: 8218
ሀ/ ይዞታ የሚተላለፍበት መንገድ፤
1.ባለይዞታ የሆነ ሰው ይዞታውን በቀጥታ ለሌላ ሰው ሲያስተላልፍ (ርክክብ ሲፈፀም ጊዜ) (ፍ/ሕግ ቁ. 1143)
2.የባለይዞታነት መብት ስለመኖሩ የሚያረጋግጡ ሰነዶች አዲሱ ባለይዞታ ለሚሆኖው ሰው በማስረከብ። ይኸውም ንብረቱ በሰነዱ ላይ ግልፅ በሆነ ሁኔታ ተዘርዝሮ ሊተላለፍ ይገባል። ይህ ዓይነት የመተላለፍያ መንገድ በተለይ በመጓጓዥ ውል (Bill of Lading) አማካኝነት ለሚተላለፉ ንብረቶች /ዕቃዎች/ ይመለከታል። /ፍ/ሕግ ቁ.1144(1) ይመለከተዋል/። ዕቃውን የሚመለከት ሰነድ በያዘና ዕቃውን በአካል በቁጥጥሩ ስር ባደረገ ሰው መካከል ክርክር የተነሳ እንደሆነ ክፉ ልቦና ወይም ተንኰል ከሌለው በስተቀር ዕቃውን በእጅ ያደረገ /ባለይዞታ/ ሰው ብልጫ /ቅድሚያ መብት/ ያገኛል። /ፍ/ሕር ቁ.1144(2) ይመለከተዋል/።
3.የቀድሞ ባለይዞታ ንብረቱ የያዝሁት ወደ ፊት አዲስ ባለይዞታ ለሚሆነው ሰው ነው ብሎ በማያጠራጥር /ግልፅ በሆነ ሁኔታ/ የገለፀ እንደሆነ ነው። /Constructive transfer/ ይሉታል። (ፍ/ሕግ ቁ. 1145(1))። ያም ሆኖ ግን የቀድሞ ባለይዞታ የከሰረ እንደሆነ ወደፊት አዲስ ባለይዞታ ለሚሆኖው ሰው ነው የያዝሁት ቢልም ከእርሱ ገንዘብ የሚጠይቁ ሰዎች መብት እንደተጠበቀ መሆኑን ሕጉ ያመለክታል (ፍ/ሕግ.1145(2) )
ለ/ ይዞታን የማስተላለፍ አስፈላጊነት፤
የይዞታ መብት የማስተላለፍ አስፈላጊነት የባለሃብትነት መብት ለማስተላለፍ ወይም ንብረቱ በሌላ ሰው እጅ ሆኖ እንዲጠቀምበትና እንዲገለገልበት ለማድረግ ወይም የእዳ መያዣ እንዲሆን ለማድረግ ይጠቅማል።
የባለቤትነት/ባለሃብትነት/መብት ለማስተላለፍ የሆነ እንደሆነ ይዞታ ከተላለፈበት ጊዜ ጀምሮ ሃሓላፊነትም አብሮ የሚተላለፍ ይሆናል። በሌላ አባባል የዕቃው ርክክብ ከተፈፀመበት ጊዜ ጀምሮ የጉዳት ሃላፊነትም አዲስ ባለሃብት ለሚሆኖው ሰው አብሮ ይተላለፋል (ፍ/ሕግ ቑ.2324 (1))
የይዞታ መብት ማስከበርያ መንገዶች፤
በአንድ ንብረትና በባለቤቱ ወይም በባለይዞታ መካከል ያለውን ግንኙነት ሕግ እውቅና ሰጥቶ ከማንኛውም ሰው የሚመጣን ሕገ ወጥ ጣልቃ ገብነት ቅሚያ በመከላከል ሕግ ጥበቃ ያደርጋል። ሕግ ለንብረት መብት ጥበቃ በማድረግ ሊደርስ የሚፈልግበት ግብ ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን በመንከባከብ ሰዎች ጥሪቶችን በተቀላጠፈ ሁኔታ ለመጠቀም እንዲችሉ የሚያነሳሳቸው ይሆናል። በመሆኑም ከንብረቱ ጋር በሕግ ተቀባይነት ያለው ግንኙነት ያለው ሰው ባገኘው የንብረት መብት ላይ ሌላ ሰው ጣልቃ በሚገባበት ጊዜ የንብረት መብት ማስከበሪያ የሆኑ መንገዶችን በመጠቀም የንብረት መብቱ እንዲከበርለት ማድረግ ይችላል።
አንድ ባለይዞታ መብቱን በሁለት መንገድ ማስከበር ይችላል።
- (1)ባለይዞታ በንብረቱ ላይ የተፈጠረን ሁከት ለማስወገድ ሓይል ተጠቅሞ ለመከላከል ይችላል። ይኸውም ንብረቱን ከነጣቂ ወይም በድብቅ ከሚወሰድ ሰው ማስለቀቅ ይችላል። በይዞታ ላይ የሚፈጠር ሁከት በሓይል ለመከላከል ግምት ውስጥ መግባት ያለባቸው ሁኔታዎች ኣሉ።
ሀ/ በሓይል የመከላከል፣ የተወሰደብህ ንብረት የማስመለስ፣ ህውከት የማስወገድ መብት ተግባራዊ መሆን የሚገባው ለችግሩ ምክንያት በሆነው ወይም ችግሩ በፈጠረው ሰው ላይ እንጂ በሶሰተኛ ወገን ላይ ተፈፃሚ ሊሆን እንደማይገባው፣
ለ/ ሓይል የመጠቀም መብት ከደረሰው ችግር ተመጣጣኝ መሆን እንዳለበትና ልኩን አልፎ መሄድ የተከለከለ መሆኑን፣
ሐ/ ለመከላከል ብሎ ሓይል የመጠቀም ተግባር ወዲያውኑ ለመከላከል ምክንያት የሆነው ችግር እንደተፈጠረ መሆን እንዳለበት ነው። እነዚህ ሁኔታዎች በወንጀል ሕግ አንቀፅ 78-ከተደነገገው-የመከላከል-መብት-ጋር የጠበቀ ቁርኝት ያለው ይመለላል።
በግል የመከላከል መብት የተቃጣን ጥቃት ለመከላከል ይቻል ዘንድ ባለይዞታው ሓይል ሊጠቀም የሚችልበትን ሁኔታ በፍ/ሕግ ቁጥር 1148(1) እና (2) ላይ ተደንግጎ ይገኛል። ይኸውም፦
“1. ባለይዞታ የሆነ ሰው እንዲሁም ለሌላ ሰው የያዘው ቢሆንም ይዞታውን ለመንጠቅ ወይም
በይዞታው ላይ ሁከት ለማንሳት የሚያደርገውን ማንኛውንም ሓይል በመከላከል ለመመለስ
መብት ኣለው።
2. እንዲሁም እጅ ያደረገው ነገር በንጥቂያ ወይም በስውር የተወሰደበት እንደሆነ ነጣቂውን
በማስወጣት ወይም ነገሩን በግፍ ሲወስድ ከተገኘው ወይም ይዞ ሲሸሽ ከተያዘው ነጣቂ ሰው
ላይ ወዲያውኑ በጉልበት በማስለቀቅ የተወሰደበትን ነገር ለመመለስ ይችላል።” ይላል።
የተቃጣን ጥቃት በመመለስ ህይወት፣ ኣካልን ወይም ሌላ ማናቸውም ፍትሓዊ መብት (legally protected right) በመከላከል ማስቀረት የመቻል መብት ህገወጥ ጥቃትን በሚያወግዝ ጠቅላላ መግባቢያ ላይ የቆመ ነው። በመሆኑም ከጥቃት ወይም ከሕገ ወጥ ድርጊት የራስን ይዞታ በመከላከል አጥቂውን መመለስ ወደ ፍርድ ቤት ሳይኬድ መብትን የማስከበርያ መንገድ (extra-judicial remedy) ነው።
ስለዚህ በሕግ በተደነገገው መሰረት የባለይዞታነት መብት ያለው ሰው በይዞታው ላይ የመንጠቅ ወይም ሁከት የማንሳት የሓይል እርምጃ ሲቃጣበት ከወንጀል ሕግም ሆነ ከፍትሓብሔር ሕግ ድንጋጌዎች ባገኘው መብት መነሻ ባለመብቱ በሓይልና ራሱን የመርዳት (self-help) መብት ይኖረዋል።
ሓይልን ሓይል በመጠቀም የመመለሱ ሁኔታ በተለይም ጉዳዩን ለፍ/ቤት ለማቅረብ ዳኝነት ለመጠየቅ ጊዜ በማይኖርበት አጋጣሚ ብቸኛ አማራጭ ይሆናል። በዚህም ባለመብቱ ለራሱ ጉዳይ ዳኛ በመሆን የተቃጣበትን ጥቃት ለመመለስ የሚወስደው እርምጃ በሕግ ተቀባይነት አለው።
በይዞታ ላይ የሚፈጠር ሁከት በፍርድ ስለማስወገድ
በሕጋዊ ይዞታው ላይ ሁከት የተፈጠረበት ወይም ከሕግ ውጭ ንብረቱ የተወሰደበት ሰው ጉዳዩን ለፍርድ ቤት በማቅረብ በይዞታው ላይ የተፈጠረው ሁከት እንዲወገድ ወይም የተነጠቀው ንብረቱ እንዲመለስ በመጠየቅ የክስ አቤቱታ ሊያቀርብ ይችላል።
በፍ/ብሔር ሕግ ቁ.1149 ላይ ስለ ሁከት ማስወገጃ ክስ እንደሚከተለው ተመልክቷል፦
“1. ይዞታው የተወሰደበት ወይም በይዞታው ላይ ሁከት የተነሳበት ሰው የተወሰደበት ነገር እንዲመለስለት ወይም የተነሳው ሁከት እንዲወገድለት እንዲሁም ስለደረሰበት ጉዳት ኪሳራ እንዲሰጠው ለመጠየቅ ይችላል።
2. የያዘው ነገር ከተነጠቀበት ወይም በይዞታው ላይ ሁከት ከተነሳበት ቀን አንስቶ እስከ ሁለት ዓመት ድረስ በፍርድ ካልጠየቀ እጅ ይዛወርልኝ የማለት ክስ መብቱ ይቀርበታል።
3.ተከሳሹ የሰራውን አደራረግ የሚፈቅድ ለርሱ የሚናገለት መብት መኖሩን በፍጥነት እና በማይታበል ዓይነት ካላስረዳ በቀር ዳኞቹ የተወሰደው ነገር እንዲመለስ ወይም የተነሳው ሁከት እንዲወገድ ያዛሉ።”
ከተጠቀሰው ድንጋጌ ይዘት መረዳት እንደሚቻለው ሁከት ለማስወገድ በፍ/ብሔር ሕግ ቁ.1149 መሰረት የሚቀርብ የክስ ኣቤቱታ (possessory action) ይዞታን የመከላከል ግብ አለው። የይዞታ መብት የሕግ ጥበቃ ስለሚደረግለትም በሕግ ላይ የተደነገገውን ስርዓት በመከተል ሌላ ባለመብት ነኝ የሚል ወገን መብቱን ከሚያስከብር በስተቀር ሓይልን በመጠቀም ባለይዞታውን ማስለቀቅ በሕግ ተቀባይነት አይኖረውም።
የዳኝነት ተቋማትም የሓይል ጥቃት ሰለባ ሆነው የባለይዞታነት መብታቸውን ከሕግ ውጭ የሚያጡ ሰዎች የሚያቀርቡትን የሁከት ማስወገጃ ክስ የተፋጠነ ሁኔታ በማየት ውሳኔ ለመስጠት ካልቻሉ ሕገ ወጥነትን ለመከላከልም ሆነ ለማስወገድ ያላቸው ብቃት የተዳከመ ይሆናል። በተለይም ሁከት ከመፈጠሩ በፊት በባለይዞታው በኩል ሁከቱ ሊፈጠር መሆኑን ከሚያስረዳ ማሰረጃ ጋር ለፍ/ቤት የቀረበ የሁከት ይወገድልኝ ክስ በሁለቱ ወገኖች መካከል የሓይል ተግባራት ተፈፅሞ የሕ/ሰቡ ሰላምና ደህንነት ከመረበሹ አስቀድሞ የዳኝነት ተቋሙ ተገቢውን የሕግ ማስከበር ሃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት ይጠበቅበታል። የሁከት ድርጊቱ ከተፈፀመ በኃላ ሰሚቀርብ የሁከት ማስወገጃ ክስ የተከሳሹ የሓይል ተግርባር መፈፀም ያለመፈፀምና የከሳሹን ይዞታ መንጠቅ ያለመንጠቅ ተገቢውን ስነ-ስርዓት ተከትሎ መጣራትና በፍጥነት ውሳኔ ማግኘት ያለበት ጭብጥ ነው።
በመሆኑም በፍ/ብሔር ሕግ ቁ.1149 (3) አነጋገር ተከሳሹ የስራውን አደራረግ የሚፈቅድለት ለርሱ የሚናገርለት መብት (right) መኖሩን በፍጥነት እና በማይታበል ዓይነት (forthwith and conclusively) ማስረዳት የሚጠበቅበት መሆኑን ስለሚያሳይ የማስረዳት ሸክሙና የጊዜውን አጠቃቀም ፍርድ ቤቶች ከግንዛቤ ማስገባት የሚጠበቅባቸው ይሆናል።
ከሁከት ማስወገጃ ክሶች አንፃር በፍርድ ቤቶች መካከል የአፈፃፀም ልዩነት ይታያል። የክሱን ይዘት የባለቤትነት መብት ማረጋገጫ አድርጎ መመልከት እንደሌሎች ጉዳዮች መደበኛውን ስነ-ስርዓት ተከትሎ መምራት እና የጉዳዮችን የተፋጠነ መፍትሄ ፈላጊነት ትኩረት ያለመስጠትና የማስረዳት ሸክሙን የትኛው ወገን መወጣት እንዳለበት የተለያዩ አቋሞችን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል።
ለማጠቃለልያህል በዚህ ምእራፍ ስር ለማየት እንደተሞከረው የይዞታ ትርጉም አንድ ሰው አንድን ነገር በእጁ አድርጎ በእውነት የሚያዝበት ሆኖ ሲገኝ ማለት እንደሆነ፣ ይዞታ ስለመኖሩ የሚያረጋግጡ ሁለት ነገሮች እንዳሉ፣ አንደኛው ንብረቱ እጅ ማድረግ ሲሆን ሁለኛው ደግሞ ንብረቱ ለመቆጣጠርና ለመጠቀም ሓሳብ መኖር ሲሆን የሁለቱ ነገሮች መምሟላት ይዞታን የሚያስገኙ እንደሆኑ አይተናል:: ይዞታ ሊቀር የሚቸለውም በባለይዞታው ፈቃድ ለሌላ ሰው የተላለፈ እንደሆነ፣ ባለይዞታ የመሆን ሓሳብ ቢኖርም ነብረቱ የጠፋ እንደሆነ እና ንብረቱ ከእጁ በይወጣም ባለይዞታ የመሆን ሓሳብ የጠፋ እንደሆነ መሆኑን ተገነዝበናል:: ይዞታ ቀጣይነተ የሌለው፣ በሓየል የተገኘ፣ በድብቅ የተያዘ እና እውነተኛ ይዞታ ስለመኖሩ የሚያጠራጥር በሆነ ጊዜ ይዞታው ጉድለት ያለበት ነው እነደሚባልም አይተናል:: የይዞታ መብት የሕግ ጥበቃ ያስፈለገበት ዋና ምክንያት እያንዳንዱ ዜጋ ወይም ሕ/ሰብ በአጠቃላይ ንብረቱን በሰላም እንዲጠቀምበተና እንዲገለገልበት ለማድረግ መሆኑን ተረድተናል:: ነገሩን በቀጥታ በመስጠት ወይም ይዞታ ስለመኖሩ የሚየረጋግጡ/የሚያስረዱ/ ሰነዶችን በማስረከብ ይዞታን ማሰተላለፍ እነደሚቻልም ለማየት ሞክረናል:: የይዞታ መብት አንደየሁኔታው በሓይል ወይም በፍርድ ቤት አማካኝነተ ማስከበር የሚቻል መሆኑንም ለመገንዘብ ችለናል::