- Details
- Category: Employment and Labor Law
መግቢያ
አንድ አሠሪ በየትኛውም ሁኔታና ዋጋ ቢሆን ከፍ ያለ ትርፍ የማግኘት ፍላጐት አለው፡፡ ሠራተኛው በሌላ በኩል ሰብዓዊ ክብሩና የሥራ ደህንነቱ ተጠብቆ የሚሠራበት ጊዜና ሁኔታ ተመቻችቶለት ለጉልበቱ ተገቢ የሆነ ክፍያ እንዲያገኝ ይፈልጋል፡፡ እኒህ ተቃራኒ የሆኑ ፍላጐቶች በአሠሪውና በሠራተኛው መካከል አለመግባባትን የመፍጠር ኃይል ያላቸው ሲሆን ችግሩን በመፍታት ረገድ ሁሉም ወገን ያሻውን እንዲያደርግ መፍቀድ የኢንዱስትሪ ሰላምን በማናጋት ቀና የሆነ የኢኮኖሚ ሂደት እንዳይኖር የሚያደርግ ነው፡፡ ስለሆነም አለመግባባቶቹ ሥርዓት ባለው መንገድ የሚፈቱበትን የህግ መንገድ ማዘጋጀት ይገባል፡፡ ይህ ማለት የህብረተሰቡን ሰላምንና ደህንነት ለመጠበቅና የኢኮኖሚ ሂደቱን ቀና ለማድረግ በሁለቱም ወገኖች ሊወሰዱ ስለሚገባቸው ዕርምጃዎች፤ ስለዕርምጃዎቹ ማዕቀፍ፤ መቼ እና እንዴት በየትኞቹ ሥራዎች ላይ መፈፀም እንዳለባቸው የህግ ቁጥጥር የሚያስፈልገው ጉዳይ ነው፡፡
በመሆኑም ያለመግባባቶች መፍቻ መሣሪያ ይሆናሉ ተብለው በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ላይ የተጠቀሱት የስራ ማቆም እና የሥራ መዝጋት እርምጃዎች ናቸው [አንቀጽ 157] ፡፡ ሁለቱም አንዱ ወገን በሌላው ላይ የኢኮኖሚ ጫናን በማሣደር አንዱ ሌላውን ለጥያቄው ተገዢ እንዲሆን የሚያደርግበት መሣሪያ ነው፡፡ ዝርዝሩን እንደሚከተለው እናያለን፡፡
የሥራ ማቆም ርምጃ
የስራ ማቆም ርምጃ ሠራተኞች የሥራ ሁኔታን በተመለከተ ከአሠሪው ጋር በሚኖራቸው አለመግባባት በአሠሪው ላይ የሥራ ማቀዝቀዝ ዘዴን በመጠቀም ወይም ሥራ በማቆም በሥራ ውጤታቸው በሚጠቀመው አሠሪ ላይ የኢኮኖሚ ጫናን በማሳደር የመደራደር አቅማቸውን የሚያጎለብቱበት መሣሪያ ነው፡፡ ይህ የሥራ ማቆም መብት በዚህ ሞጁል መጀመሪያው ክፍል እንዳየነው ሕገ-መንግስታዊ መሠረት ያለው ሲሆን ሠራተኞች ሌሎች መብቶቻቸውን ጭምር ስራ ላይ ለማዋል አስፈላጊ መሳሪያ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
ሥራ ማቆም ማለትም ቁጥራቸው ከአንድ በላይ የሆኑ ሠራተኞች በኀብረት በመሆን የአሠሪና ሠራተኛን ክርክር በሚመለከት ጉዳይ አሠሪያቸው ማናቸውንም ዓይነት የስራ ሁኔታን እንዲቀበል በግድ ጥቅምን ወይም የሚፈልጉትን ውጤት ለማግኘት ተጽዕኖ በማድረግ ከአሠሪው ፍለጐት ውጪ ለጊዜው ከመደበኛው የሥራ መጠን እና መደበኛው የሥራ ውጤት እንዲቀንስ ሥራቸውን በማቀዝቅዝ ወይም ባለመስራት የሚወስዱት ርምጃ ነው [አንቀጽ136] ፡፡
በዚህ ትርጓሜ ውስጥ የሚከተሉትን ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ የሥራ ማቆም በአሰሪና በሠራተኛ መካከል በሚፈጠር አለመግባባት ሠራተኞች ፍላጐታቸውን ለማስፈፀም እንደመፍትሄ መሣሪያነት የሚጠቀሙበት መንገድ መሆኑን፤ ለርምጃው መሠረት የሚሆኑት እንደ የትርፍ ሰዓት ክፍያ፣ የዕረፍት ሰዓት፣ ቦነስና የመሣሠሉት ዓይነት የሥራ ሁኔታዎች መሆናቸውን፤ ርምጃው በየግል አቋም የሚወሰድበት ሣይሆን በሕብረት ያለመግባባት ምከንያት በሆኑት ነጥቦች ላይ ምን፣ መቼ እና እንዴት ማድረግ እንዳለባቸው ሠራተኞች አቋም የሚወስዱበት እንደሆነ፤ በተገለፀው መንገድ በህብረት አቋም የተያዘበት ውሣኔ ቀጥተኛ ውጤቱ ሥራን በማቀዝቀዝ ወይም በማቆም ላይ መሆን እንዳለበት እና ይህም ከአሠሪው ፍለጐት ውጪ እንደሚፈፀም የመጨረሻ ግቡም የኢኮኖሚ ጫናን በአሠሪው ላይ በማሣደር ጥያቄያቸውን ወይም የመደራደሪያ ነጥባቸውን እንዲቀበል ማስገደድ እንደሆነ ማጤን ሊነሱ የሚችሉትን ውዝግቦች ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመፍታት ይረዳል፡፡
የስራ ማቆም ርምጃ የሚገለጥባቸው መንገዶች [አንቀጽ 158 (1)]
የሥራ ማቀዝቀዝ- ማለት በመደበኛው ሁኔታ ሥራው ቢከናወን ሊገኝ የሚችለው ውጤት እንዳይኖር ማድረግ ነው፡፡ ሠራተኞች ሥራቸውን ይሠራሉ ነገር ግን በሚፈለገው ፍጥነት እና የመሥራት አቅም አይደለም፡፡ እንዲህ ያለው ዕርምጃ በኢኮኖሚ ላይ የሚያሣድረው ጫና ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ የተወሰነ ውጤትን ለማግኘት የሚጠይቀውን የማምረቻ ዋጋ ከፍ ያደርጋል፣ ጥሬ ዕቃዎችና ማሽነሪዎች ከአቅማቸው በታች እንዲሠሩ በማድረግም ጥቅም የመስጠት አቅማቸውን ይቀንሣል፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ የስራ ማቀዝቀዝ እርምጃ እንደ አንድ አማራጭ በሥራ ማቆም ርምጃ ሥር መገኘቱ ግር የሚያሰኝ ሊሆን ይችላል፡፡ ይሁንና በአንቀጽ 158 ላይ እንደተገለፀው ሥራ ማቆም በከፊል ሊሆን እንደሚችል ከመገለፁ አንፃር ይህ የሥራ ማቀዝቀዝን ይመለከታል ማለት ይቻላል፡፡ ስለሆነም የሥራ ማቀዝቀዝ ግብ የታለመው መደበኛ ውጤት እንዳይኖር ማድረግ በመሆኑ በከፊል ሥራውን የማቆም ያህል ኃይል አለው፡፡ በዚህ የተነሣ የሥራ ማቀዝቀዝ በሥራ ማቆም ርምጃ ሥር መምጣቱ ተገቢ ይመስላል፡፡
የሥራ ማቆም- ይህ ሠራተኞች ሥራቸውን ላለመሥራት በመወሰን ሥራ የሚያቆሙበት ሁኔታ ነው፡፡ በዚህ ውሣኔ መሠረት ወደ ሥራ ቦታቸው ላይሄዱ ይችላሉ፤ ቢሄዱም ሥራቸውን ላይሠሩ፤ በመስሪያ ቤቱ ቅጥር ግቢ ወይም በአካባቢው ሊቆዩ ይችላሉ፡፡ በየትኛውም መንገድ ግን ለጥያቄያቸው አሠሪው ተገቢውን መልስ እንኪሰጥ ድረስ ሥራቸውን እንደተቋረጠ የሚቀጥል ነው፡፡
የሥራ ማቆም ርምጃ ለመውሰድ ማሟላት ያለባቸው ሁኔታዎች [አንቀጽ158 (1) (3)]
የስራ ማቆም ርምጃ ከፍ ሲል እንደተጠቀሰው በኢንዱሰትሪ ሰላምና በኢኮኖሚ ላይ ጫናን የሚያደርስ ነው በመሆኑም በቂ ዝግጀት እንዲደረግበና መፍትሔ እንዲገኝለት ውጤታማ መንገድ ለማፈላለግ እንዲቻል ርምጃው ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት ሊከተላቸው የሚገባ ሥርዓቶች አሉ፡፡ የመጀመሪያው ርምጃው የጋራ መብትን የሚመለከት በመሆኑ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የሠራተኛ ማኀበር አባላት ቢያንስ በ2/3ኛው በተገኙበት በአብዛኛው የተደገፈ መሆን አለበት፡፡ 2/3ኛ የተባለው ውሣኔውን ለማሣለፍ በአካል የሚገኙት አባላት ቁጥርን የሚመለከት እንጂ ሳይሳተፉም ድጋፋቸውን በሚያገኙ በሁለት ሶስተኛው የተደገፈ ማለት አይደለም፡፡ በአካል ከሚገኙት 2/3ኛው ወስጥ በአብዛኛው የሥራ ማቆም ርምጃውን ከደገፉት በቂ ይሆናል፡፡
በአብላጫው ድምፅ የተደገፈው የሥራ ማቆም ውሣኔ ለሥራ ማቆሙ ምክንያት ከሆኑት ሁኔታዎች ጋር በግልጽ ተጽፎ ርምጃው ከመወሰዱ ከ10 ቀን በፊት ለአሠሪው እና በአካባቢው ለሚገኘው የሠራተኛ እና ማኀበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ ወይም አግባብ ላለው የመንግስት መስሪያ ቤት ይሰጣል፡፡ ይህ ሲሆንም ሁለቱም ወገኖች በመካከላቸው ያለውን ልዩነት በስምምነት ለመጨረስ ጥረት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ የድርጅቱ የደህንነት መመሪያዎችና የአደጋ መከላከያ ዘዴዎች በሠራተኛው መጠበቅ አለባቸው፡፡
እኒህ ሁኔታዎች የተሟሉ ቢሆንም፤ ክርክሩ ለአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ ወሣኝ ቦርድ ወይም ለፍርድ ቤት ቀርቦ ውሣኔ ሣይሰጥበት 30 ቀን ከማለፉ በፊት ወይም ፍ/ቤት ውሣኔ ሣይሰጥበት በሕግ የተወሰነው የጊዜ ገደብ ከማለፉ በፊት የስራ ማቆም ርምጃ መውሰድ ህገ-ወጥ ነው፡፡ ቦርዱ ወይም ፍርድ ቤቱ የሥራ ክርክርን ጉዳይ በሙሉ ወይም በከፊል ለመጨረስ ያሣለፈውን ትዕዛዝ ወይም ውሣኔ አለመቀበል፣ ወይም ለውሣኔው በሚፃረር አኳኋን የሥራ ማቆም ርምጃ መውሰድ ወይም የፍርድ ቤቱን ወይም የቦርዱን ትዕዛዝ ሣይፈጽሙ ማዘግየት ህገ-ወጥ ይሆናሉ፡፡ ይህም ሲባል ቦርዱ ወይም ፍርድ ቤቱ የሰጠውን ውሣኔ በሥራ ላይ እንዲውል ለማስገደድ የሚወሰደው ሥራ ማቆም ህገ-ወጥ አይሆንም፡፡ ሌላው የሥራ ማቆሙ ርምጃ ከአመጽ፣ ከግዙፋዊ ኃይል ወይም ዛቻ ወይም በግልጽና በይፋ ሕገ-ወጥ አድራጐት ጋር የተፈፀመ እንደሆነ ህገ-ወጥ ይሆናል፡፡
የሥራ ማቆም ርምጃ ተፈፃሚ የማይሆንባቸው ድርጅቶች
የሥራ ማቆም ርምጃ የሚያስከትለው ውጤት በተዋዋይ ወገኖች ላይ የኢኮኖሚ ጫና በማሣደር ብቻ የሚገታ አይደለም፡፡ ዳፋው በሥራው መቀጠል ምክንያት የሚጠቀመውን ህዝብ በጠቅላላው የሚያውክ ይሆናል፡፡ በተለይም እጅግ አስፈላጊ የሕዝብ አገልግሎት በሚሰጡ ተቋማት ላይ የሥራ ማቆም ርምጃ ቢወሰድ ከፍ ያለ ጉዳትን የሚያመጣ ነው፡፡ ለምሣሌ ያህል በሆስፒታል የሚሠሩ ሠራተኞች የሥራ ማቆም ርምጃ ቢወስዱ በህዝብ ጤንነት ላይ ሊደርስ የሚችለውን ችግር የሚያስከትለውን ውስብስብ ተፅዕኖ መረዳት የሚያስቸግር አይሆንም፡፡
ስለሆነም እጅግ አስፈላጊ ናቸው የተባሉ የሕዝብ አገልግሎት በሚሰጡ ተቋማት ላይ የሥራ ማቆም እርምጃ መውሰድ በኢኮኖሚ፣ በጤና፣ በደህንነት ላይ የሚደርሰውን ከፍ ያለ ጉዳት ለማስቀረት በማሰብ በአንቀጽ 136/2/ ላይ ሥራ ማቆም የማይፈቀደባቸው ድርጅቶች ተዘርዝረዋል፡፡ እነኚህም
- የአየር መንገድ አገልግሎት
- የኤሌክትሪክ መብራትና ኃይል አገልግሎት የሚሰጡ ድርጅቶች
- የውሃ አገልግሎት የሚሰጡ እና የከተማ ጽዳት የሚጠብቁ ድርጅቶች
- የከተማ አውቶብስ አገልግሎት
- ሆስፒታሎች፣ ክሊኒኮች፣ የመድኃኒት ማከፋፈያ ድርጅቶችና የመድኃኒት መሸጫ ቤቶች
- የእሣት አደጋ አገልግሎት እና
- የቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት ናቸው፡፡
የሥራ መዝጋት ርምጃ
ትርጓሜ፡-
የሥራ መዝጋት ዕርምጃ የኢኮኖሚ ጫና በመፍጠር ፍላጎታችንን የምናስፈጽምበት መሳሪያ ነው፡፡ ሥራ መዝጋት ማለት
"የአሠሪና ሠራተኛን ክርክር በሚመለከት ጉዳይ ሠራተኞች አንድ ዓይነት የሥራ ሁኔታን እንዲቀበሉ ለማስገደድ ወይም በግድ ለማግባባት፣ ጥቅምን ወይም የሚፈለገውን ውጤት ለማግኘት የሥራ ቦታን በመዝጋት የሚፈፀም የኢኮኖሚ ተፅዕኖ ነው"
በዚህ ትርጉም ሥራ የመዝጋት ዕርምጃን የሚያቋቁሙት
- በአሠሪና በሠራተኛው መሃል ያለመግባባት መኖር፤ የስራ ቦታን በመዝጋት የኢኮኖሚ ጫና የመፍጠር ኃይል ያለው አሰሪው ሲሆን ይህን የሚያደርገውም በሠራተኞች ላይ ነው፡፡ ስለሆነም አለመግባባቱ ተቃዋሚ ፍላጎት ባላቸው ሁለቱ ክፍሎች ነው ማለት ነው፡፡
- አለመግባባቱ የሠራ ሁኔታን የሚመለከት መሆኑ፡- አሠሪና ሠራተኛውን የሚያነታርከው ማናቸውም ጉዳይ ሳይሆን እንደ ‘የሠራ ሰዓትን፣ ደመወዝን፣ ሠራተኞች ከሥራ በሚሰናበቱበት ጊዜ የሚገባቸውን ክፍያዎች፣ ጤንነትና ደህንነትን፣ በሥራ ምክንያት ጉዳት ለደረሰባቸው ሠራተኞች የሚከፈለውን ካሳ፣ ሠራተኞች ከሥራ የሚቀነሱበትን ሁኔታ፣ የቅሬታ አቅራረብ ሥርዓቶችንና የመሳሰሉትን የሥራ ሁኔታን’ የሚመለከቱ ነጥቦች ናቸው፡፡
- አሠሪው ሠራተኞችን የማስገደድ ወይም በግድ እንዲቀበሉት የማድረግ ፍላጎት ያለው መሆኑ፤ እዚህ ላይ የአሰሪው ፍላጎት ጫናን በማሳደር ፍላጎቱን ማስፈፀም ወይም እንዲቀበሉት ማድረግ በመሆኑ ርምጃው በጊዜያዊነት የሚፈጸም እንደሆነ መረዳት ይቻላል፡፡ በሌላ አባባል ከሠራተኞች ጋር ያለውን ግንኙነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የሚቆርጥ እንደማባረር ያለ ዕርምጃ አይደለም ማለት ነው፡፡ በጊዜያዊነት ከሚወሰዱት እንደማገድ ያሉ ዕርምጃዎች አንፃር ሲታይም ይህ የብዙሃኑን ጥቅም የሚመለከት እና የጋራ በሆኑት የሠራተኞች ጉዳዮች ላይ ቀድሞውኑም ያለተግባቡበት ነጥብ መኖሩን የሚያሳይ ነው
- ርምጃው የሥራ ቦታን በመዝጋት በሠራተኞች ላይ የኢኮኖሚ ጫና ለማሳደር የሚፈፀም መሆኑ ሌላው ነጥብ ነው፤ የሥራ ቦታው የሚዘጋው በሙሉ ወይም በከፊል ሊሆን ይችላል፡፡ በሙሉ መዝጋት ድርጅቱን በጠቅላላው የሥራ እንቅስቃሴ እንዳይኖረው ማድረግ ነው፡፡ በከፊል መዝጋቱ ግን የድርጅቱን የተወሰኑ ክፍሎች ብቻ እንዳይሰሩ ማድረግ ነው፡፡
የሥራ መዝጋት ርምጃ ለመውሰድ መሟለት ያለባቸው ሁኔታዎች
አንድ አሠሪ የሥራ መዝጋት ዕርምጃ ከመውሰዱ በፊት ሊከተላቸው የሚገቡ ሥርዓቶች አሉ፡፡ ከነኚህ ውስጥ የመጀመሪያው ላለመግባባት ምክንያት በሆኑት ጉዳዮ ላይ በታቸለ መጠን ስምምነት እንዲፈጠር ለማድረግ ጥረት ማድረግ ይገባቸዋል፡፡ ሳይቻል የቀረ እንደሆነ ሥራ ለመዝጋት አሰሪው ሲወስን ምክንያቱን በመዘርዘር ለሰራተኞች ማኅበር እና በአካባቢው ለሚገኘው ለሚኒስቴሩ ተወካይ ወይም አግባብ ላለው የመንግስት መስሪያ ቤት ሥራ ለመዝጋት መወሰኑን ሥራውን ከመዝጋቱ አስር ቀን ቀደም ብሎ መስጠት አለበት፡፡ ይህ ሲሆንም በአሰሪውም ሆነ በሠራተኞች የድርጅቱ የደኅንነጽ መመሪያዎችና የአደጋ መከላከያ ዘዴዎች እንዲጠበቁ ያስፈልጋል፡፡
የተከለከሉ ድርጊቶች
የሥራ ማቆምም ሆነ የሥራ መዝጋት እርምጃ የሚወስድ ወገን ጉዳ ለሚመለከተው ሌላው ወገን እና በአካባቢው ለሚገኘው ለሚኒስቴሩ ተወካይ ወይም አግባብ ላለው የመንግስት መስሪያ ቤት እርምጃው ከመወሰዱ ከ10ቀን በፊት መሰጠት አለበት፡፡ የይ ሳይፈጸም እርምጃ መውሰድ የተከለከለ ነው፡፡ [159 cum 160(1)] ፡፡ እንዲሁም የሥራ ክርክር ለአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ ወሳኝ ቦርዱ ወይም ለፍርድ ቤት ከቀርበ በኋላ
- ቦርዱ ትዕዛዝ ወይም ውሳኔ ሳይሰጥበት 30 ቀን ካላለፈ በቀር
- ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሳይሰጥበት በህግ የተወሰነው የጊዜ ገደብ ካላለፈ በቀር ዕርምጃውን መውሰድ የተከለከለ ነው፡፡ ‘ውሳኔ ሳይሰጥበት በህግ የተወሰነው የጊዜ ገደብ’ ማለቱ ፍርድ ቤት ጉዳዩ ከቀረበለት በኋላ በስልሳ ቀን ውስጥ እንዲወስን በህግ ግዴታ አለበት፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች በዚህ ጊዜ ውስጥ መወሰን የማይችልበት ሁኔታ ቢፈጠር የትኛውም ወገን ዕርምጃውን ለመውሰድ የሚችለው ከዚህ ጊዜ በኋላ ብቻ ይሆናል፡፡
- ቦርድ ወይም ፍርድ ቤት ያሳለፈው ውሳኔ ካለም ይህንኑ ማክበር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ውሳኔውን አልቀበልም ማለት፣ባለመቀበልም የስራ ማቆም ወይም የሥራ መዝጋት ዕርምጃ መውሰድ፣ ወይም ትዕዛዙን ወይም ውሳኔውን ሳይፈፅሙ ማዘግየት የተከለከለ ተግባር ነው፡፡ ነገር ግን ትዕዛዙን ሳይፃረሩ የተፈረደበት ወገን ትዕዛዙን ወይም ውሳኔውን ዕንዲፈፅም ለማስገደድ ከሆነ ህገ ወጥ ተግባር አይሆንም፡፡
ከዚህ በተረፈም ዕርምጃዎቹ ከግዙፋዊ ኃይል ወይም ዛቻ ወይም በግልፅና በይፋ ሕገ-ወጥ ከሆነ አድራጎት ጋር መፈጸም የተከለከለ ነው፡፡
- Hits: 16255
- Details
- Category: Employment and Labor Law
በልዩ ግዴታ ምክንያት የሚሰጡ አገልግሎቶች
የስራ ጉዳት በደረሰ ጊዜ አሠሪው ልዩ ግዴታዎች አሉበት፡፡ ይኸውም በጊዜው
- የህክምና ዕርዳታ መሥጠት
- ተስማሚ በሆነ የመጓጓዣ ዘዴ በአቅራቢያው ወደሚገኘው የህክምና ጣቢያ ማድረስ እና የሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር በሚያወጣው መመሪያ መሠረት የሥራ ላይ ጉዳት መድረሱን ማሳወቅ እንዲሁም ጉዳቱ
- እንዲሁም ጉዳቱ ሞትን ባስከተለ ጊዜ የቀብር ሥነ ሥርዓት ወጪውን መሸፈን ናቸው፡፡
የሕክምና አገልግሎቶች
- ከፍ ሲል ከተገለፁት ክፍያዎች በተጨማሪ ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ የሚያስፈልገው የጠቅላላ እና የልዩ ሕክምና እንዲሁም የቀዶ ህክምና ወጪዎች፣ የሆስፒታል እና የመድኃኒት ወጪዎች፤ የማናቸውም ሰው ሰራሽ ምትክ ወይም ተጨማሪ አካሎችና የአጥንት ጥገና ወጪዎች በሙሉ በአሰሪው ይሸፈናሉ፡፡ ይህ ሲሆን የህክምና አገልግሎቱ ቦርድ በሚሰጠው ውሣኔ መሰረት ካልሆነ በቀር አገልግሎት መሰጠቱ የሚቋረጥ አይሆንም፡፡
ልዩ ልዩ የጥሬ ገንዘብ ክፍያዎች
ሀ. ለጊዚያዊ የአካል ጉዳት የሚፈፀም ክፍያ
ጊዜያዊ የአካል ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ ጉዳቱ እስከሚወገድበት ጊዜ ድረስ በየጊዜው የሚፈፀምለት ክፍያ አለ፡፡ “ጉዳቱ እስከሚወገድበት ድረስ” የሚለው ሐረግ በየጊዜው የሚፈፀመው ክፍያ ከአንድ ዓመት የበለጠ እንደማይሆን በአንቀጽ 108(1) እና 108(3)(ሐ) ከተገለፀው አንፃር እንድምታው ምን ይሆናል የሚል ጥያቄ ሊያስነሳ ይችላል፡፡ ተገቢም ነው፡፡ “ጉዳቱ እስከሚወገድበት ድረስ” የሚለው ጊዜያዊ የአካል ጉዳት በባህሪው ጉዳቱ ለአጭር ጊዜ ብቻ የሚዘልቅና ሠራተኛው የመሥራት ችሎታውን መልሶ የሚያገኝ ስለመሆኑ ግምት መወሰዱን፤ ከዚህ በላይ የተራዘመ እንደሆነ ግን አግባብ ባለው ባለሥልጣን ወይም በአንዱ ወገን ጠያቂነት በድጋሚ በሚደረገው ምርመራ ውጤቱ ታይቶ የተጐጂ የጉዳት መጠን ደረጃ ወደ ሌላው ደረጃ በመሻገርም ቢሆን ክፍያው በዚያው አግባብ ሊፈፀምለት እንደሚችል ወይም እንደሚፈፀምለት የሚያመለክት ነው ብሎ ማሰብ ትክክል ሳይሆን አይቀርም፡፡ በየጊዜው የሚደረገው ክፍያ የተባለውም
- ጉዳቱ ከደረሰ ጀምሮ ላሉት የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ጉዳቱ ከመድረሱ በፊት ሠራተኛው ያገኝ የነበረውን የአመቱ አማካይ ደመወዝ ሙሉ ደመወዝ
- ከዚህ በኃላ ላሉት ሦስት ወራት ደግሞ ጉዳቱ ከመድረሱ በፊት ሠራተኛው ያገኝ የነበረውን የአመቱን አማካዩ ደመወዝ 75% እና
- ለቀሪዎቹ ስድስት ወራት ጉዳቱ ከመድረስ በፊት ሠራተኛው ያገኝ የነበረው የአመቱ አማካይ ደመወዝ 50% ነው፡፡
ይህ በየጊዜው የሚደረገው ክፍያ የሚያቆመው
- ሠራተኛው የደረሰበት ጉዳት የተወገደለት መሆኑን ሐኪም ሲያረጋግጥ
- ሠራተኛው የጉዳት ጡረታ ወይም ዳርጐት በሚያገኝበት ቀን
- ሠራተኛው ሥራ ለመሥራት ካቆመበት ዕለት ጀምሮ አሥራ ሁለት ወር ሲሞላው ነው፡፡
የተገለፁት ሁኔታዎች ከመድረሳቸው አስቀድሞ ተጐጂው በማናቸውም ጊዜ ምርመራ እንዲደረግለት ሲጠይቅ እምቢተኛ ከሆነ፣ ቸል ያለና ምርመራውን ያደናቀፈ፣ ያለበቂ ምክንያት እንዲጓተት ያደረገ፤ ከጉዳቱ የሚድንበትን ጊዜ ለማራዘም በማሰብ አጉል ጠባይ ያሳየ ወይም ጉዳት ስለደረሰባቸው ሰራተኞች የወጣውን መመሪያ የተላለፈ እንደሆነ በየጊዜው የሚደረግለት ክፍያ ይቋረጣል፡፡ ለጥያቄው ተገቢ መልስ እስኪሠጥም ይኸው ይቀጥላል፡፡ በዚሁ ግፊት ምክንያትም ፍቃደኛ ሲሆን በተቋረጠበት ጊዜ ያልተከፈለውን ክፍያ መልሶ አያገኝም፡፡ [አንቀጽ 107 (2) (3)]
ለዘላቂ ሙሉ ወይም ከፊል የአካል ጉዳት የሚፈፀም ክፍያ
ለዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት የሚፈፀመው ክፍያ በሕብረት ሥምምነት በሌላ አኳኃን ካልተወሰነ በቀር በአሠሪና ሠራተኛው አዋጅ መሰረት ለሚሸፈኑ የመንግሥት ድርጅት ሠራተኞች አሠሪው የገባው የመድኅን ዋስትና ካለ በዚሁ መሰረት ክፍያው ይፈፀማል፡፡ ድርጅቱ መድኀን ያልገባ እንደሆነ ደግሞ በመንግሥት የጡረታ ሕግ መሠረት ክፍያው ይፈፀማል፡፡ ይህ አከፋፈል በመንግሥት የጡረታ ህግ ለማይሸፈኑ ሠራተኞችም ተፈፃሚ ነው 109 ፡፡ ልዩነቱ በመንግሥት የጡረታ ህግ የማይሸፈኑት ተጐጂ ሠራተኞች ክፍያው የሚፈፀምላቸው በአንድ ጊዜ (in lump sum) መሆኑ ብቻ ነው፡፡ ክፍያው በተገለፀው ሁኔታ በአንድ ጊዜ የሚከፈል በሚሆንበት አጋጣሚ የጉዳቱ ካሣ መጠን ለዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት የሠራተኛው የዓመት ደመወዝ በአምስት ተባዝቶ፤ ጉዳቱ ከዛላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት መጠን በታች እንደሆነም በተመሣሣይ ሁኔታ ነገር ግን ከአካል ጉዳቱ ደረጃ ጋር የተመጣጠነ ክፍያ ይሆናል፡፡ በቀኝ እጅ ላይ የደረሰው ጉዳት 70% ቢሆን ለዚሁ ጉዳት መጠን ተመጣጣኝ የሆነ ክፍያ እንደማለት ነው፡፡
በሞት ምክንያት ለጥገኞች የሚፈፀም ክፍያ
በደረሰው ጉዳት ምክንያት አንድ ሠራተኛ ወይም ለማጅ ሠራተኛ የሞት አደጋ የደረሰበት እንደሆነ በዚሁ ምክንያት በሟቹ ጥገኝነት ሥር የሚተዳደሩ ሰዎች የጉዳት ካሣ ክፍያ ይፈፀምላቸዋል፡፡ በሟቹ ሥር የሚተዳደሩ የሚባሉትም
- የሟቹ ባል ወይም ሚስት
- ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ልጆች
- በሟቹ ድጋፍ ይተዳደሩ የነበሩ የሟች ወላጆች ናቸው
ሟቹ ሠራተኛ በመንግሥት የጡረታ ህግ የማይሸፈን በሆነ ጊዜ ለጥገኞቹ ለሚፈፀመው ክፍያ መሠረት የሚሆነው የሟቹ ሠራተኛ የአመት ደመወዝ በአምስት ተባዝቶ የሚገኘው የገንዘብ መጠን ነው፡፡ ታዲያ ይህ ሲሆን ለሚስት ወይም ለባል የዚህ ደመወዝ 50%፣ ዕድሜያቸው 18 ዓመት ላልሞላቸው ልጆች ለእያንዳንዳቸው 10% ፣ ለሟች ወላጆች ለእያንዳንዳቸው 10% የበለጠ ወይም ያነሰ መሆን የለበትም፡፡ አንድ ልጅ ያለው ባል ቢሞት ለሚስቱ 50% ለልጁ 10% ሲሰጥ በድምሩ 60% ማለት ነው፡፡
መጠኑ 100% መሆን ስላለበት በያንዳንዱ ድርሻ ላይ እንደድርሻቸው መጠን ቀሪውን 40% ማደላደል አለብን ወይም ይኖርብናል፡፡ በተመሣሣይ ሁኔታም ልጆቹ በዝተው መጠኑ ከ100% ያለፈ እንደሆነም ከፍ ሲል የተገለፀውን ዘዴ በመጠቀም መጠኑን ወደ 100% ዝቅ እንድናደርግ ይጠበቅብናል፡፡
ከዚህ በተረፈ በጉዳት ምክንያት የሚገኙ ክፍያዎች ከገቢ ግብር ነፃ ናቸው፡፡ ለሌላ የሚተላለፉ፣ ሊከበሩ ወይም በዕዳ ማቻቻያነት ሊያዙ የማይችሉ ናቸው፡፡
- Hits: 13535
- Details
- Category: Employment and Labor Law
የአካል ጉዳት መጠን ደረጃዎች
የአካል ጉዳት መጠን ደረጃዎች በአራት ይከፈላሉ፡፡ ይኸውም
- ጊዜያዊ የአካል ጉዳት
- ዘላቂ ከፊል የአካል ጉዳት
- ዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት እና
- ሞት ናቸው፡፡ እንደየቅደም ተከተላቸው በሚከተለው ሁኔታ እናያቸዋለን፡፡
ሀ. ጊዜያዊ የአካል ጉዳት፡-
የዚህ ጉዳት ሰለባ የሆነ ሠራተኛ የተመደበበትን ሥራ ለተወሰነ ጊዜ በሙሉ ወይም በከፊል ለማከናወን እንዳይችል ይሆናል አንቀጽ (100)፡፡ የመሥራት ችሎታው መቀነስ ወይ መጥፋት ጉዳቱን ለመጠገን በሚወስደው ጊዜ ይገደባል፡፡ ከዚያ በኋላ የመሥራት ችሎታው ይመለሳል፡፡ በአብዛኛው የጊዜው ርዝማኔ ከአንድ ዓመት የሚዘል አይሆንም፡፡ ለዚህ መነሻ የሚሆነው በአንቀጽ 107(1) cum 108(1) እና 108(3)(ሐ) ላይ የተገለፀው ነው፡፡ ጊዜያዊ የአካል ጉዳት እስከሚወገድበት ጊዜ ድረስ ተገቢው ክፍያ ሲፈፀም ቢቆይም ይህ በየጊዜው የሚሰጠው ክፍያ ከአንድ ዓመት የሚዘል አይሆንም [አንቀጽ 108(1)]፡፡ ይህ ማለት ጊዜያዊ የአካል ጉዳት ከአንድ ዓመት ያለፈ የመሥራት ችሎታን የሚያሳጣ አይደለም የሚለውን ሐሳብ የሚያመጣ ነው፡፡
ለ. ዘላቂ ከፊል የአካል ጉዳት ፡-
ይህ ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ የማይድን እና የመሥራት ችሎታውን የሚጐዳ ችግር ይገጥመዋል [አንቀጽ 101(1)] ፡፡ የመሥራት ችሎታው መቀነስ ለተመደበበት ሥራ ብቻ ሳይሆን በተመሣሣይ ሥራ ላይ ያለውን የመሠራት ችሎታ ጭምር የሚመለከት ነው፡፡ በያዘው የሥራ መደብ ላይ መሥራቱን ቢቀጥልም ባይቀጥልም የመሥራት ችሎታው አንድ ጊዜ የቀነሰ እና አብሮት የሚዘልቅ በመሆኑ መለኪያው ይሠራ የነበረው ሥራ ብቻ አይሆንም፡፡ በሌላ ቦታ በሌላ ጊዜና ሁኔታ ሊሠራ ይችል ለነበረው ለዚያው ሥራ ያለውን አቅም የሚያዳክም በመሆኑ ይኸው ግምት ውስጥ የሚገባ ይሆናል፡፡
ሐ. ዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት
ይህ ጉዳት ደግሞ ማናቸውንም ደመወዝ የሚያስገኝ ሥራ ለመሥራት የሚከለክል የማይድን ጉዳት ነው [አንቀጽ 101 (2)] :: ከፍ ብሎ ከተገለፀው ዘላቂ ከፊል የአካል ጉዳት ይህ በሁለት ዐቢይ ነጥቦች የሚለይበትን ሀሳብ ይዞ ቀርቧል፡፡ የመጀመሪያው የጉዳቱ መጠን መለኪያ ሆኖ የቀረበው ገቢ የማግኘት እንጂ የመሥራት ችሎታው አቅም አለመሆኑ ነው፡፡ በከፊል ዘላቂ የአካል ጉዳት የመሥራት ችሎታ መቀነስ የገቢ መቀነስን የሚያስከትል ቢሆንም ሁል ጊዜ ይህ ይሆናል ማለት አይቻልም፡፡ የመሥራት ችሎታው ቀንሶ እያለ በዚያው ደመወዝ ወይም ሻል ባለ ደመወዝ ሊሠራ የሚችልበት አጋጣሚ ሊኖር ይችላል፡፡ ይህ ግን ሁኔታውን አይለውጠውም፡፡ ዋናው መለኪያ የገቢው አለመነካት ወይም ከፍ ማለት ሳይሆን የመሥራት አቅሙ (Potential) መቀነስ ነው በዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት ግን መሠረታዊው ጉዳይ ገቢ የማግኘ አቅምን ማሳጣት ነው::
ሌላው ደግሞ በዘላቂ ከፊል የአካል ጉዳት የመሥራት ችሎታው መቀነስ በመደበኛ ሁኔታ የገቢ ሁኔታን የሚቀንስ ሲሆን ይህ የገቢ መቀነስ የሚታየው ሠራተኛው ይሠራ ከነበረው ወይም በተመሣሣዩ ሁኔታ ሊሠራ ይችል ከነበረው ሥራ አንፃር ነው፡፡ ለዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳት መሠረት የሚሆነው ግን ሠራተኛው ማናቸውንም ገቢ የሚያስገኝ ሥራ ለማግኘት የሚከለክለው መሆኑ ነው፡፡ እዚህ ላይ “ማናቸውንም ደመወዝ የሚያስገኝ ሥራ” የሚለው ምን ማለት ነው? የሚለውን ማየት ይገባል፡፡ “ማናቸውንም” የሚለው ቃል ሰፋ ባለ መንገድ ታይቶ ሠራተኛው ከጉዳቱ በፊት ከነበረው ሙያ ውጪ ያሉ ሥራዎችንም እንደሚሸፍን ለምሳሌ አንድ ማሽኒስት የነበረ ሰው “በተሸካሚነት” ወይም “በሊስትሮነት” ሥራ ላይ ተሠማርቶ መሥራት ከቻለ ዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳተኛ ሊባል አይችልም የሚል ትርጉም እንደሚሰጥ ማንበብ አለብን ወይስ ጉዳቱ በደረሰ ጊዜ ተጐጂው በቀጥታ ወይም በተለዋዋጭ ሊሠራ ይችል ከነበረው የሠለጠነበት ወይ የተማረበት አማራጭ የሥራ መስኮች አንፃር መታየት አለበት? የፊተኛው ትርጓሜ እጅግ ሰፊ ከመሆኑ የተነሣ ተጐጂዎች ሁሉ ከፍ ሲል ከተጠቀሱት ዓይነት ሙያዎች በአንዱ ሊሠማሩ የሚችሉ መሆናቸው ብቻ ከዘላቂ ሙሉ የአካል ተጐጂነት ሽፋን በርካታዎችን የሚያወጣ ይሆናል፡፡ ስለሆነም ዘላቂ ሙሉ የአካል ጉዳተኛ አይኖርም ወይም ቁጥራቸው ያንሳል፡፡ ይህ ግን በጉዳቱ ከፍተኛነት የተነሣ በዘላቂ ሙሉ የአካል ተጐጂነት መደብ ሊያገኙ የሚገባውን ክፍያ እንዳያገኙ የሚያደርግ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ይልቁንም የሠራተውኛው ጉልበት ለዕድገት መሠረት መሆኑን ከግምት የሚያስገባወና ተገቢውን ክብር የሚሰጠው፣ ተመዛዛኝ (efficient) እና ተግባራዊ (Pragmatic) የሆነው አተረጓጎም ጉዳቱ በደረሰ ጊዜ ሠራተኛው በቀጥታ ወይም በተለዋዋጭ ሊሠራ ይችል ከነበረው የሠለጠነበት ወይም የተማረበት አማራጭ የሥራ መስኮች አንፃር ማየቱ ሳይሆን አይቀርም፡፡
መ. ሞት፡-
ይህ ጉዳት ደግሞ በአንድ ሠራተኛ ላይ ሊደርስ የሚችለው አስከፊው እና የመጨረሻው ደረጃ ነው፡፡ ጉዳቱ ራሱን የሚገልጽ በመሆኑ ማብራራያ የሚያስፈልገው አይደለም፡፡
የጉዳት መጠን አወሳሰን
በአንድ ሠራተኛ ላይ የሚደርሱት የጉዳት መጠን ደረጃዎች ከፍ ብለው የተገለፁት ናቸው፡፡ ይህን ደረጃ በመመሪያ በጉዳት መወሰኛ ሠንጠረዥ የሚያወጣው የሠራተኛ እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ነው ፡፡ ደረጃ የሚያወጣው ለዘላቂ ከፊል እና ሙሉ የአካል ጉዳት ብቻ ነውአንቀፅ 102 1፡፡ በጊዜያዊ የአካል ጉዳት ሠራተኛው ቀድሞ የነበረውን የመሥራት ችሎታ መልሶ ስለሚያገኝ፤ ሞትም ቢሆን የጉዳቱ መጠን በራሱ የተገለጠ በመሆኑ ሚኒስትሩ ለነዚህ ጉዳቶች ደረጃን አይወስንም፡፡
ደረጃቸውን ለሚወስንላቸው ዘላቂ ሙሉ ወይም ከፊል ጉዳቶች ግን የጉዳቶቹ መጠን ደረጃ ከመወሰኑ በፊት ጉዳቱ በደረሰ በአስራ ሁለት ወራት ውስጥ በተቻለ መጠን የጉዳቱን መጠን መወሰን ከሚኖርበት የህክምና ቦርድ ማስረጃ ማግኘት ይጠይቃል [አንቀጽ 102 (2)] ፡፡
በዚህ መንገድ የጉዳቱ መጠን እና ደረጃ ከተወሰነ በኋላ ውሳኔው ቋሚ ሆኖ የሚቀጥል ላይሆን ይችላል፡፡ የጉዳቱ መጠን ከውሳኔው በኋላ ከፍ ሊል ወይም ሊሻሻል ይችላል፡፡ ይህን ለማድረግ የሚያበቃ ምክንያት አለ ወይም ቀድሞ የተደረገው ምርመራ ሥህተት አለበት የሚል ወገን ወይም አግባብ ያለው ባለሥልጣን ሲጠይቅ በዚሁ መነሻነት በድጋሚ ምርመራ ሊደረግ ይችላል፡፡ አንቀጽ 102 (3) በድጋሚ ምርመራው የጉዳቱ መጠን ከተለወጠ ደረጃው በዚያው መጠን ታርሞ በጉዳቱ ምክንያት የሚገኘው ክፍያ እንዲቀጥል፣ እንዲጨምር ወይም እንዲቀንስ ይደረጋል [አንቀጽ 102 (4)(5)] ፡፡ ለምሳሌ ያህል ጊዜያዊ የአካል ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ ከአንድ ዓመት የሚዘልቅ የመሥራት ችሎታን የሚቀንስ ጉዳት ያገኘው እንደሁ ተጐጂው በሚያቀርበው ጥያቄ መነሻነት በድጋሚ ተመርምሮ ወደሚቀጥለው ደረጃ ሊሻገር ይችላል፡፡ የሚፈፀመው ክፍያም በዚሁ መጠን የሚስተካከልለት ይሆናል፡፡
- Hits: 14002
- Details
- Category: Employment and Labor Law
ትርጉም
በሥራ ምክንያት የሚመጣ በሽታን ትርጉም ማወቅ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ ከበሽታዎች ውስጥ የትኛው በስራ ምክንያት እንደሚመጣ የትኞቹ ደግሞ በተለመደው ሁኔታ የሰውን ልጅ የሚያጠቁ ከሥራ ጋር ያልተያያዙ እንደሆኑ ለመለየት ይረዳል፡፡ በኢትዮጵያ አሠሪና ሠራተኛ ህግ መሠረት በሥራምክንያት የሚመጣ በሽታ ማለት
“ሠራተኛው ከሚሠራው የሥራ ዓይነት ወይም ሠራተኛው ከሚያከናውነው ሥራ አካባቢ የተነሣ በሽታው ከተከሰተበት ዕለት አስቀድሞ በነበረው የተወሰነ ጊዜ ውስጥ በፊዚካል፣ ኬሚካል ወይም ባዮሎጂካል ነገሮች አማካኝነት በሠራተኛው ላይ የሚደርስ የጤና መታወክ ነው” [አንቀጽ 98(1)]
በዚህ ትርጉም የሥራ ላይ በሽታው ምክንያት
- የሥራው ዓይነት ነው
- የሥራው አካባቢ ሁኔታም ነው፡፡
በሁለቱም መንገዶች ቢሆን በሽታው ከሥራው ጋር ግንኙነት አለው፡፡ ከሌሎች በሽታዎች የሚለየውም በሽታው ለሥራው የተለመደ ወይም የሚታወቅ ውጤትን የሚያስከትል መሆኑ ነው፡፡ አስም ማንኛውንም የህብረተሰብ ክፍል የሚያጠቃ ቢሆንም ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ለረጅም ጊዜ የሠራ ሰው ለዚህ በሽታ የተጋለጠ ነው፡፡ይህ የሆነውም በሥራው ዓይነት ምክንያት ነው፡፡ በተመሣሣይ ሁኔታም ከፍተኛ ድምጽ ያለበት ቦታ የሚሰራ ሰው የመስማት ሀይሉ ሊቀንስ ወይም ላይኖር ይችላል፡፡ ስለሆነም በእንዲህ ያሉ ሁኔታዎች የሚመጣው በሽታ “የሥራ ላይ በሽታ” ሲባል ተጠቂ ለመሆን ያበቃው ምክንያትም የሥራው ዓይነት ነው ማለት ይቻላል፡፡
የሥራው አካባቢ ሁኔታ ስንልም በሽታው ከሥራው ጠቅላላ ባህሪ የሚመነጭ ወይም በሥራው ባህሪ ምክንያት የሚመጣ ሳይሆን ሠራተኛው እንዲሠራ የሚጠበቅበትን የሥራ ተግባር ተደጋጋሚ በሆነ የማከናወን ሂደት ሲፈጽም ለአንድ ወይም ለሌላው በሽታ የሚጋለጥበት አጋጣሚ ማለት ነው፡፡ በምሳሌ ለመግለጽ ያህል አንድ የቀበሌ የህብረት ሱቅ ሠራተኛ ቆሻሻ የሚቃጠልበት ቦታ አካባቢ ለረጅም ጊዜ በመስራቱ የአስም በሽተኛ ሆኗል፡፡ የህብረት ዕቃዎች መሸጥ በመደበኛ ሁኔታ የአስም በሽታን አያስከትልም፡፡ ሠራተኛው ለዚህ ችግር የተጋለጠው እንዲሠራ የተመደበበት የሥራ አካባቢ ሁኔታ በበሽታው ለመጠቃት ምክንያት ስለሆነው ወይም ተጋለጭነቱን ስላሰፋው ነው፡፡ ስለሆነም በተመሣሣይ ሁኔታ የሥራ አካባቢ ሁኔታዎች በመደበኛ ሁኔታ ችግሩን ያስከትላሉ ባይባልም እንደተጠቀሰው ባለ ልዩ አጋጣሚዎች በሥራ ምክንያት ለሚመጣ በሽታ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ ማለት ነው፡፡
የሥራ ላይ በሽታዎችን በተመለከተ የሠራተኛ እና ማሕበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ሚኒስቴር አግባብ ካለው ባለሥልጣን ጋር በመምከር በሥራ ምክንያት የሚመጡ በሽታዎችን ዝርዝር በመመሪያ እንዲያወጣ ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ይህ ዝርዝር በየአምስት ዓመቱ ሊሻሻል የሚችል ነው፡፡ ዝርዝሩ በጅምላ የሚወጣ ሳይሆን እንደየሥራ ባህሪው እየተለየ የሚገለፅ ነው፡፡ ለአንዱ የሥራ መስክ የሥራ ላይ በሽታ የሚባለው ለሌላው የሥራ መስክ የሥራ ላይ በሽታ ላይባል ይችላል፡፡ ስለሆነም ዝርዝሩ ከየሥራ መስኮቹ ባህሪ አንፃር እየታየ የሚዘጋጅ ነው፡፡
ዝርዝሩ ከተዘጋጀ በኃላ በዝርዝሩ ውስጥ ካሉት ባንዱ በሽታ የተጠቃ ሰው በሽታው እንዳለበት ሲረጋገጥ የሥራ ላይ በሽታ እንደያዘው ማስረጃ ሊሆነው ይችላል፡፡ ከተገለፁት ውጪ በሆነ በሽታ የተጠቃ ሰው ግን
- የተጠቃው በሥራ ላይ በሽታ ስለመሆኑ
- ለተገለፁት በሽታዎችም ቢሆን መንስኤ ናቸው የተባሉት ችግሮች ሌላ መገለጫ ያላቸው ስለመሆኑ ማስረጃ በማቅረብ የሥራ ላይ በሽታ ተጠቂ መሆኑን የማስረዳት ዕድል አለው፡፡
ይህ ብቻም አይደለም፡፡በዝርዝሩ ውስጥ የተካተተ ባይሆን እንኳን ተቃራኒ ማስረጃ ካልቀረበ በአንድ የተወሰነ ስራ ላይ የተሰማሩ ሰዎችን ብቻ በተደጋጋሚ የሚይዝ በሽታ አንድን ሰራተኛ የያዘው መሆኑ ሲታወቅ የተጠቃው በስራ ላይ በሽታ እንደሆነ ይቆጠርለታል፡፡ ይህ በራሱ (prima facie) በሽታው ከስራው ጋር አንድ አይነት ትስስር እንዳለው ማስረጃ ነው፤ በስራው እና በበሽታው መካከል ያለውን ግንኙነት በጊዜው የቴክኖሎጂ ደካማነት የተነሣ መረዳት በማይቻልበት ሁኔታ በሰራተኛው ላይ የሚደርሰው ጉዳት ሣይካስ እንዳይቀር ለማድረግ ይህ ጥሩ መንገድ ነው፡፡
የቴክኖሎጂው ዕድገት የሣይንሱን ምጥቀት እየተከተለ ዝርዝሩ በየአምስት ዓመቱ እንዲዘጋጅ መደረጉም ከማስረጃ አቀራረብ አንፃር ሰራተኛው በቀድሞው ዝርዝር ውስጥ ያልነበሩትን የስራ ላይ በሽታዎች ለማስረዳት የሚኖርበትን ችግር የሚያቃልልለት ነው፡፡
የስራ ላይ በሽታ የደረሰበትን ጊዜ ስለመወሰን
ስለበሽታው ከፍ ሲል በተገለፀው መንገድ ከተነጋገርን አሁን ደግሞ የስራ ላይ በሽታው መቼ እንደደረሰ መነጋገሩ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ በጉዳቱ ምክንያት የሚገኘውን የካሣ ጥያቄ ለማቅረብ የሚቻል መሆን አለመሆኑን ለመወሰን፤ መጠየቅ የሚቻል ሲሆን እንኳን የካሣው ተጠቃሚ ለመሆን ጥያቄው በምን ያህል ጊዜ መቅረብ እንዳለበት ለመወሰን ይረዳል፡፡
ስለሆነም በስራ ምክንያት በሚመጣ በሽታ ጉዳት የደረሰበት ዕለት በሽታው በግልጽ የታወቀበት ቀን ይሆናል፡፡ በሽታው በግልጽ ታውቋል የሚባለውም
- ሰራተኛው የመስራት ችሎታውን ያጣበት ቀን
- በሽታው በሐኪም ተመርመሮ መኖሩ የታወቀበት የመጀመሪያው ዕለት
- ሰራተኛው በበሽታው ምክንያት የሞተበት ዕለት ነው፡፡
እነኚህ ሁኔታዎች ሰራተኛው በበሽታው የተያዘበት ጊዜያት እንደሆኑ ይቆጠራል፡፡ “እንደሆነ ይቆጠራል” መባሉም በሽታው በአንድ ጊዜ የሚከሰት ሣይሆን በሂደት የሚገለጥ በመሆኑ ትክክለኛውን በበሽታው የተለከፈበትን ዕለት ማወቅ አስቸጋሪ በመሆኑ ነው፡፡
በሥራ ምክንያት በሚመጣ በሽታ ጉዳት የደረሰበትን ዕለት ስንወስን ይህን ተከትሎ የሚመጣው የመጀመሪያው ጥያቄ ሠራተኛውን በሽተኛ ለማድረግ ያበቃው ሰበብ በሽታው ከተከሰተበት ዕለት አስቀድሞ በምን ያህል ጊዜ ውስጥ የተፈጠረ መሆን አለበት የሚለው ነው፡፡ ይህን ለመመለስ ወደ ትርጓሜው መለስ ስንል በሽታው ከተከሰተበት ዕለት አስቀድሞ በነበረው የተወሰነ ጊዜ ውስጥ በፊዚካል፣ ኬሚካል ወይም ባዮሎጂካል ነገሮች አማካኝነት የሚደርስ የጤና መታወክ ሲል ይገልፀዋል “የተወሰነ ጊዜ ውስጥ” የሚለው እንደየበሽታው ጠባይ ሊለያይ የሚችል በመሆኑ ወጥ የሆነ ጊዜ ማስቀመጥ አይቻልም፤ ግን ደግሞ ይህን የተወሰነ ጊዜ ልክ ማን ይወስናል? ሚኒስትሩ መመሪያ እንደሚያወጣ የተነገረው በስራ ምክንያት የሚመጡ በሽታዎችን ዝርዝር ነው፡፡ እነኝህ የተዘረዘሩ በሽታዎች በምን ያህል ጊዜ ሲከሰቱ የስራ ላይ በሽታ እንደሚሆኑ ሊወስን እንደሚችል የተገለፀ ነገር የለም፡፡ ስለሆነም ይህ ጊዜ በሐኪሞች እንዲረጋገጥ የተተወ ነው? ወይስ የማሕበራዊና ሠራተኛ ጉዳይ ሚኒስትር የስራ ላይ በሽታን ዝርዝር ሲያወጣ በሽታው በስራ ምክንያት የመጣ ነው ለማሰኘት አንዱ አስፈላጊ ነገር የበሽታው በተወሰነ ጊዜ ውስጥ መገለጥ ጭምር በመሆኑ ሚኒስትሩ ይህን ጊዜ ከሚመለከተው አካል ጋር በመነጋገር ከዝርዝሩ ጋር አብሮ ያወጣዋል? ክርክር በተፈጠረ ቁጥር ሐኪሞች በየጊዜው እየተጠየቁ የሚሰጡት ማረጋገጫ ሣይሆን በኃለኛው መንገድ የሰራተኛ እና ማሕበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር የሥራ በሽታ ዝርዝርን ሲያወጣ አብሮ ጊዜውን የሚወስን እንደሆነ ማሰቡ ትክክለኛው መስመር ይመስላል፡፡
ሌላው ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነሣው ጥያቄ ሰራተኛው በአንድ በሽታ የተለከፈው ሰራተኛ ከመሆኑ በፊት የሚሆንበት አጋጣሚ ነው፡፡ ሰራተኛ ከመሆኑ በፊት የተለከፈ ሰው ሰራተኛ ከሆነ በኃላ የሚሰራው ስራ ለበሽታው መባባስ ምክንያት በሚሆንበት ጊዜ በሽታው የሥራ ላይ በሽታ ሊባል ይችላል ወይ? የሚለው ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ በተወሰነ ጊዜ ውስጥ የሚለው የተለከፈበትን ወይስ የተባባሰበትን ዕለት ማለት ነው? አንድ ምሣሌ ለመጨመር ያህል ለሶስት ዓመት በጨርቃ ጨርቅ ፋበሪካ ውስጥ የሰራ ሰው የአስም በሽታ ሊይዘው እንደሚችል ቢገለጽና አንድ ስራተኛ በሁለተኛ ዓመቱ ለዚሁ በሽታ በተፈጥሮው በቀላሉ የሚጠቃ በመሆኑ በሁለተኛ ዓመቱ በአስም ቢያዝና ይህም ሦስት ዓመት ከመሙላቱ በፊት ቢታወቅ የሥራ ላይ በሽታ አይባልም፡፡ በሽታው እየተባባሰ በመሄዱ ግን በአራተኛ ወይም በአምስተኛ ዓመቱ የተመደበበትን ሥራ ለመሥራት እንዳይችል ቢሆን የተባባሰው በዝርዝሩ ከተወሰነው ጊዜ በፊት በመሆኑ ብቻ የተባባሰበትን ጊዜ ከግምት ሳናገባ በጉዳቱ ምክንያት የሚያገኘውን ክፍያ ማሳጣት ተገቢ ይሆናል?
- Hits: 15779